«በሰንበት ኢየሱስ መጻጉዕን ተነሥ አልጋህን ተሸከም ባለው ጊዜ ቀኑ ሰንበት ነበረ፡፡ መጻጉዕም አልጋውን ተሸክሞ ወደ ቤቱ ገባ የእግዚአብሔር ልጅ በሰንበት ፈውሷልና
«በሰንበት ድውያንን ፈወሰ የዕውራንንም ዓይኖች አበራ እያለ 38 ዓመት በአልጋ ቁራኛ በደዌ ዳኛ ተይዞ ሲማቅቅ የኖረውን መጻጉዕንና ሌሎቹን በልዩ ልዩ ደዌ የተያዙትን ሕሙማን መፈወሱን በጠቅላላው ለምፅ ማንጻቱን፣ ዕውር ማብራቱን፣ አንካሶችን ማርታቱን፣ ልምሾዎችን ማዳኑን፣ አጋንንትን ማውጣቱን፣ወዘተ እየጠቃቀሰና እያነሣሣ ስለሚዘምር ዕለቱና ሳምንቱ መጻጉዕ ተብሏል፡፡
ስለዚህም ይህ ሰንበት የሕሙማን ፈውስ መታሰቢያ ዕለት ነው ማለት ይቻላል፡፡ በነዚህ ሁሉ ታሪኮች የመጻጉዕንና የሌሎቹን ሕሙማን ሁሉ ደኅንነት ታሪክ እንረዳለን፡፡ የሰንበቱም ስያሜ ልብ ወለድ አጠራር ሳይሆን የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢርና የጾመ ድጓውን ይትበሀል ተከትሎ የተሰየመ መሆኑን እንገነዘባለን፡፡
በዕለቱ በቅዳሴ ላይ የሚነበቡትም ምንባቦች የሚከተሉት ናቸው፡
1ኛ. የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ወደ ገላትያ ሰዎች 5Ý1(26
2ኛ. የሐዋርያው የቅዱስ ያዕቆብ መልእክት 5፡14-20
3ኛ. የሐዋርያት ሥራ 3፡1-12
በመዝሙር 4ዐቁጥር 3 ላይ የሚገኘው
እግዚአብሔር በደዌው አልጋ ላይ ሳለ ይረዳዋል፡፡ መኝታውን ሁሉ በበሽታው ጊዜ ያነጥፍለታል እኔስ አቤቱ ማረኝ፡፡
የሚለው ይሆናል፡፡የዕለቱ የወንጌል ንባብም
በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 5 ከቁጥር 1 እስከ 25 ድረስ ያለው ነው፡፡
ያንን ተስፋ ያልነበረውን በሽተኛ ከደዌ ሥጋው ፈውሶ ሕይወትን የሰጠው አምላክ፣ እኛንም በውስጥ በአፍአ ካለብን ደዌ ሥጋና ደዌ ነፍስ እንዲፈውሰን፤ ቁስለ ኃጢአታችንን እንዲያደርቅልን፣ በሕይወትና በጤና እንዲጠብቀን የእርስ የጌታች ቅዱስ ፈቃድ ይሁንልን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር