ብፁዕነታቸው በመክፈቻው ሥነ ሥርዓት ላይ እንደ ተናገሩት “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በ2000 ዓመት የታሪክ ጉዞዋ ያለፈችበት ታሪክ ረጅም፤ ያካበተችው ዕውቀትና ትውፊት ብዙና ዘርፈ ብዙ ከመሆኑ አንጻር እንደዚህ ዓይነቱ ዐውደ ርዕይ ቤተ ክርስቲያኗን በእሷም በኩል ሀገሪቱን በማስተዋወቅ ረገድ ሰፊ ሚና ይኖረዋል፤ ዝግጅቱ በርቀት ሆኖ የኢትዮጵያን መጥፎ ገጽታ እንዲሰማ በሆነው በውጭው ዓለም መቅረቡ ደግሞ የበለጠ ደስታን ይሰጣል“ ብለዋል።
ዐወደ ርዕዩን አዘጋጅቶ ለዕይታ ያበቃውን ማኅበር በእጅጉ ያመሰገኑት ብፁዕነታቸው በመክፈቻው ላይ ለተገኙት ከ200 በላይ ለሚሆኑ ጀርመናውያንና የሌሎች ሀገራት ዜጎች በዐውደ ርዕዩ የቀረበውን የኢትዮጵያ መንፈሳዊ ታሪክ፣ ባሕል፣ ቅርስና ትውፊት በተግባር ለማየት ወደ ኢትዮያ እንዲሔዱ ጋብዘዋል::
በዚሁ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት ላይ ልጅ አስፋ ወሰን አሥራተ ካሳ የቤተ ክርስቲያ•ን ረጅም ታሪክ በጀርመንኛ ለተሰባሰቡት እንግዶች አብራርተዋል:: ማኅበሩን በመወከልም ዲ/ን መርሻ አለኸኝ ባደረገው ንግግር ማኅበረ ቅዱሳን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶሰ ዕውቅና በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ከተÌÌመበት ጊዜ ጀምሮ በሀገር ውስጥና በውጭ ሰፊ መንፈሳዊ አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ ገልጧል:: በንግግሩ ማጠቃለያም ዐውደ ርዕዩ በተሳካ ሁኔታ ይከናወን ዘንድ አስተዋጽኦ ያደረጉ ድርጅቶችንና ግለሰቦችን አመስግኖ ወደ ፊት ለሚከናወኑ ተመሳሳይ ዝግጅቶችም ድጋፋቸው እንዳይለይ አደራ ብሏል::
በርካታ ምእመናን በተገኙበት በተከናወነው የዐውደ ርዕዩ መዝጊያ ሥነ ሥርዓርት ላይ በዲ/ን አብርሃም አሰፋ አማካኝነት እንደተገለጠው ዝግጅቱ ከተጠበቀው በላይ በበርካታ ኢትዮያውያንና የውጭ ሀገር ዜጎች ተጎብኝቷል:: ከጎብኝዎቹ ውስጥ ከጀርመን ሀገር ከልዩ ልዩ ከተሞች የመጡ በርካታ ኢትዮጵያውያንና የውጭ ዜጎች እንደተገኙበት ከአስተያየት መስጫ መዝገቡ ለመረዳት ተችሏል:: በፍራንክፈርት የቀረበውን ዐውደ ርዕይ በሌሎች የአውሮፓ ዋና ዋና ከተሞችም የማቅረብ ዕቅድ እንዳለ በማጠቃለያ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ተገልጧል::
በተያያዘ ዜናም ከዐውደ ርእዩ ጋር ለማካሄድ ታቅዶ የነበረው የአንድ ሳምንት የስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር በፍራንክፈርት ቅ/ማርያ፣ኢ ቤተ ክርስቲያን ተከናውኗል። ከግንቦት 24-30 ቀን 2001ዓ.ም በተደረገው በዚህ ጉባዔ ከፍራንክፈርትና ከአካባቢው የመጡ ምእመናን የተሳተፉበት ሲሆን ምእመናኑ ይህ ዓይነቱ ጉባኤ ወደፊትም በቋሚነት እንዲከናወንላቸው በአጽንዖት ጠይቀዋል።