View in English alphabet 
 | Thursday, May 2, 2024 ..:: መቅድም ::.. Register  Login
  

ብፁዕ አቡነ ጎርጎሪዮስ ካልዕ (፲፱፻፴፪ - ፲፱፻፹፪)

የሕይወት ታሪክ እና አገልግሎታቸው

መግቢያ

ዛሬ የሚያውቋቸው ሲቃ ይተናነቃቸዋል። ዓይናቸው በእንባ ይሞላል። ስለብፁዕነታቸው ሲያወጉ ውለው ቢያድሩ አይሰለቹም። እንኳን ዘዋይ ደርሰው የመጡት ፊታቸውን እንኳን አይተው የማያውቁት የብፁዕ አቡነ ጎርጎሪዮስን ዜና ሕይወት መተረክ ያስደስታቸዋል። ለምን ይሆን? ብዙዎች በአካል ሳያውቋቸው ጣፋጭ ትምህርታቸውን ከአንደበታቸው ሳያዳምጡ በማለፋቸው ይቆጫሉ። ሌሎች ደግሞ ትምህርታቸውን፣ ምክራቸውን፣ ሓሳባቸውን ሁሉ በምስል እና በድምጽ ሳያስቀሩ በማለፋቸው ይጸጸታሉ። ሐዋርያዊ ተጋድሎዋቸው እና መንፈሳዊ አርበኝነታቸውን በቅርብ ላስተዋለ እና ዜና ሕይወታቸውን ላዳመጠ ብፁህነታቸው ዘወትር የሚነበቡ ታላቅ መጽሐፍ ነበሩ። የቅንጦት እና የቅምጥል ሕይወት ሳይናፍቃቸው በፍጹም ገዳማዊ ጠባይ የላመ የጣመ ሳይመገቡ፣ በትኅርምት እየኖሩ ወላጅ አልባ እና ችግረኛ ህጻናትን ሰብስበው እያሳደጉ ቢንቢ እየወረሳቸው ዋዕዩ  በሚፋጅበት የወባ በሽታ ባየለበት ሌላው ቀርቶ ጣፋጭ እና ንጹህ ውሃ እንኳን በማይገኝበት ስፍራ ራሳቸውን ጥለው በበሽታ ሲሰቃዩ  አንድ ቀን እንኳን ሳይሰለቹ እና ሳይማረሩ በተጋድሎ የኖሩ እጅግ ትሁት የነበሩ አባት ነበሩ። በመንፈስ የወለዷቸው፣ በሃይማኖት ያሳደጓቸው ልጆቻቸው ከልብ በመነጨ ፍጹም ፍቅር “ጎርጎሪ” እያሉ ሲጠሩዋቸው የሰማ የብፁዕነታቸውን ታሪክ ለማወቅ ይጓጓል።

 

ልደት እና አስተዳደግ

ብፁዕ አቡነ ጎርጎሪዮስ በ1932 ዓ.ም በደቡብ ወሎ ሃገረ ስብከት በደሴ ከተማ ከአቶ ገበየሁ አየለ እና ከወ/ሮ አሰለፈች ካሳ ተወለዱ። ወላጆቻቸው ወንዶች ልጆች ሲወልዱ እየሞቱባቸው በጣም ተቸግረው ስለነበር ለፈጣሪያቸው ልመና አቅርበው በስዕለት ወንድ ልጅ ወልደው ለማሳደግ በቁ። ለልጃቸው ከነበራቸው ፍቅር የተነሳም “ተስፋዬ” በማለት ስም አወጡላቸው። ብርቅዬ የስእለት ልጅ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ጎርጎሪዮስ በህጻንነታቸው ወራት የወላጆቻቸውን፣ የዘመዶቻቸውን እና የሌሎችም ሰዎች ዓይን ማረፊያ ነበሩ። ከእድሜ እኩያዎቻቸው ጋር ከቤት ወጥተው ሲጫወቱ የእንጨት መስቀል ሰርተው ጓደኞቻቸውን ለማሳለም ይሞክሩ ነበር። አንድ ቀን ብቻቸውን ሲሆኑ ደግሞ  የመምህራቸውን የአለቃ ድንቁን የድጓ መጽሐፍ ገልጠው ሲያዩ  የተመለከቱት አለቃ ድንቁ “ዕድሜ ሰጥቶኝ የዚህን ህጻን መጨረሻ ባሳየኝ” ብለው ነበር።

የትምህርት ሕይወት

ዕድሜያቸው ለት/ት ሲደርስ በደሴ መድኃኔአለም ቤ/ክ ፊደል ለመቁጠር፣ የግዕዝ ንባብ ለመማር ሄዱ። ብፁዕ አባታችንም ይህን ትምህርት ሲማሩ በቀለም አያያዛቸው የደብሩ መምህራን በጣም  ያደንቋቸው ነበር።ብፁዕነታቸው በኮከብ አዕምሮአቸው የጀመሩትን ት/ት የበለጠ ሊገፉበት ስለፈለጉ በህጻንነታቸው ት/ት ፍለጋ የተወለዱበትን መንደር፣ ያደጉበትን ቀዬ ትተው ወደ ላስታ ሄዱ። በልጅነት ዕድሜያቸው ምናኔ የጀመሩት በዚያን ጊዜ ከላስታ ወደ ደሴ መጥተው የነበሩትን አባ ክፍለ ማርያም የሚባሉትን መምህር ተከትለው ነበር። አባ ክፍለ ማርያም ከደሴ ወደ ላስታ ገነተ ማርያም፣ ነአኩቶ  ለአብ ገዳም ሲመለሱ አባ ጎርጎሪዮስ ተከትለዋቸው ላስታ በር ይደርሳሉ። አባ ክፍለ ማርያም ጸሎት ሊያደርሱ ወደ ተቀመጡበት ስፍራ ሲያመሩ አባ ጎርጎሪዮስም ቀረብ ብለው “ጤና ይስጥልኝ” ይላሉ አባ በጸሎት ሰዓት የሚያናግራቸውን ሰው የሚያናግሩት በግዕዝ  ነበር እና “መኑኬ” አሏቸው። አባ ጎርጎሪዮስም  በድንጋጤ ዝም ሲሉ ሌሎች ተማሪዎች “ማነህ” ነው የሚሉህ አሏቸው። አባ ጎርጎሪዮስም “እኔ ነኝ እርስዎን ተከትዬ ልሔድ ከደሴ መጥቼ ነው” አሉ። በዚህን ጊዜ አባ ክፍለ ማርያምም ደንገጥ በለው “እረ ሎቱ ስብሐት! ከደሴ እስከዚህ ድረስ እኛን ስትከተል!” በማለት በውሳኔያቸው ተገርመው ወደ ላስታ አባ ቡሩክ ገዳም ይዘዋቸው ይገባሉ። ደሴ የተጀመረው ትምህርት ወደ ላስታ ሲመጡ በቀላሉ የሚታለፍ አልነበረም። የተማሪ ቤት ሕይወት በትህትና የተሞላ፣ አንዱ ለሌላው ወንድሙ በመጨነቅ የሚኖርበት ሕይወት ነው። ተማሪ ቤት ምቾት በሌለው መኝታ፣ ያለመብራት በጨለማ እያፈጠጡ፣ ጠዋት ምግብ ፍለጋ ሲወጡ ከውሾች ጋር እየታገሉ በረሃብ እና በጥም፣ በወረርሽኝ እየተንገላቱ የሚማሩበት፣ ብዙ ችግር እና መከራ የሚያሳልፉበት፣ የነገውን ማንነት በብዙ ድካም የሚቀርጹበት እና ዘወትር የማይጠፉ ብዙ ትዝታዎችን የሚሰበስቡበት ሕይወት ነው። የተማሪ ቤቱን ትዝታ ብጹዕ አባታችን እራሳቸው በእንግሊዘኛ ባቀረቡት አንድ ጥናታዊ ጽሁፋቸው እንዲህ ገልጸውት ነበር።

“ለቋንቋ ዕድገት በቅድሚያ መምህር ቀጥሎም የማስተማሪያ መሳሪያዎች፣ ት/ቤት፣ ወረቀት፣ ብዕር እና ቀለም አስፈላጊ መሆናቸው ይታወቃል። ዘመናዊ የማስተማሪያ መሳሪያዎች ባልነበሩበት ጊዜ ቤተ ክርስቲያን የዛፍ ጥላዎች እና የመቃብር ቦታዎችን በት/ቤነት ተጠቅማለች። አንድ ሰው ሲሞት በቤ/ክ ግቢ ይቀበራል። ዘመዶቹም በመቃብሩ ላይ ለእንግዶች እና ለመንገደኞች ማደሪያ የሚሆን ቤት ይሰራሉ። የቀድሞ  የቤ/ክ ሊቃውንትም ሲያስተምሩ እና ሲማሩ የኖሩት እንደዚህ ባሉ የመቃብር ቤቶች ውስጥ ነበር። ወረቀት ባይኖርም ካህናቱ ፍየል እና የበግ ቆዳ እና ሌጦ አድርቀው፣ ቀፈው እና ፍቀው ብራና አዘጋጅተው ፊደል ጽፈውበታል። ገብስ ቆልተው፣ ፈጭተው፣ በውሃ በጥብጠው ከከሰል ጋር ደባልቀው ቀለም አዘጋጅተዋል። ቀጭን መቃ ቆርጠው፣ ቀርጸው፣ ጫፉን ሰንጥቀው ከቀርነ በግዑ እየጠቀሱ የሚጽፉበት ብዕር አዘጋጅተዋል። አያሌ የኢትዮጵያ መጻሕፍት የተጻፉት እንደዛሬው በኅትመት መሳሪያ ሳይሆን በሊቃውንቱ እጅ ነበር።” ብጹዕ አባታችን ከታዋቂው መምህር ክፍሌ (አባ ክፍለ ማርያም) ዘንድ የውዳሴ ማርያም እና የቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜ፣ አዕማደ ምስጢራትና ባህረ ሐሳብን ተምረዋል። ብጹዕነታቸው በተማሪ ቤት እጅግ በሚያስደንቅ ፍጥነት እና ጉጉት የሚነገራቸውን ቀለም ከመያዛቸውም ሌላ ከእርሳቸው በላይ በትምህርት የገፉት ተማሪዎች ሲማሩ በሚያደምጡት ብቻ ቀለሙን ይዘው ተማሪዎቹ ሲሳሳቱ ያርሙ እና ይመልሱ ነበር። ብጹዕነታቸው ዘወትር ጥያቄ መጠየቅ ይወዱ ስለነበር መምህራቸው የሚነግሯቸውን ሁሉ ልቅም አድርገው ይይዙ ነበር። በዚህ ችሎታቸው የተደነቁት መምህራቸው በቤተሰባቸው የወጣላቸውን ተስፋዬ ገበየሁ የሚለውን ስም መዝገበ ሥላሴ ክፍሌ በማለት በራሳቸው ስም እንዲጠሩ አድርገዋል።

ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ በዘመኑ ከነበሩት ከብጹዕ አቡነ  ይስሐቅ ማዕረገ ዲቁናን ከተቀበሉ በኋላ ሌሎች ትምህርቶችን ለመቀጸል ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም መጥተዋል። በገዳሙም በ1956 ዓ.ም ምንኩስናን ተቀብለዋል። ከምንኩስናም በኋላ ለት/ት የነበራቸው ከፍተኛ ፍላጎት እየጨመረ በመምጣቱ ወደ አዲስ ዓለም ደብረ ጽዮን ማርያም ሄደው ከታላቁ የቅኔ መምህር ከአፈወርቅ መንገሻ ዘንድ ቅኔ ከነአገባቡ ጠንቅቀዋል። ከዚያም ወደ ደብረ ሊባኖስ ተመልሰው የሐዲሳት ትርጓሜና ትምህርተ ሃይማኖት ከመምህር ገ/ሕይወት ሲቀጽሉ፣ መጽሐፈ ሊቃውንትን ደግሞ  ከመምህር ቢረሳው አሂደውታል። ቀጥሎም ወደ ደብረ ጽጌ ማርያም በመሄድ ዜማ፣ ምዕራፍ፣ ጾመ ድጓን ከመሪጌታ አብተው ላሊታግዳን መዝገበ ቅዳሴን ከመምህር ልዑል ተምረዋል።

ብጹዕነታቸው ከቤ/ክ ሊቃውንት እግር ሥር እየተቀመጡ በብዙ ድካም እና ችግር ከሃገር ወደ ሃገር እየተዘዋወሩ የገበዩት ዕውቀት ታላቅ የቤ/ክ ዓምድ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል። ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ በፍቅረ እግዚአብሔር የተቃጠሉ እጅግ ትሁት እና አስተዋይ አባት ነበሩ። በደብረ ሊባኖስ ገዳም በነበሩበት ጊዜ በዕድሜ የገፉትን መነኮሳት ሊጥ አብኩተው፣ ዳቤ ጋግረው እና ሌሎችም ተግባራት በመፈጸም ይራዱ ነበር። በብህትውና ዘመናቸው የሰገዱበት የእጃቸው ፈለግ ቀንበር የዋለበት የበሬ ጫንቃ  ይመስል እንደነበር ገዳማዊ ሕይወታቸውን በቅርብ የሚያውቁ አባቶች ይናገራሉ። በ1957 ዓ.ም ወደ አ/አ በመምጣት ከብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ማዕረገ ቅስናን ተቀብለዋል። ከዚያም ከመምህር ፍስሐ ወደ ብጹዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ተልከው ሐረርጌ በሔዱበት ጊዜ ከመንፈሳዊ ሕይወታቸው ጎን ለጎን በደሴ አቋርጠውት የነበረውን የአንደኛ እና የሁለተኛ ደረጃ ት/ታቸውን ተከታትለዋል። በዘመናዊ ት/ቤት ቆይታቸውም ሌት ተቀን ተግተው በትኩረት የሚከታተሉ መሆናቸውን ያወቁት ብጹዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ከፍተኛ ሞራል በመስጠት ይንከባከቧቸው ነበር። በተጨማሪም ወደቤታቸው እያስጠሩ ያስተምሯቸው ነበር። ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ የቁልቢ ቅዱስ ገብርኤል ቤ/ክ አስተዳዳሪ በመሆንም አገልግለዋል። የብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስን የአዕምሮ ብስለት እና ከፍተኛ የትምህርት ጉጉት የተረዱት ብጹዕ አቡነ ቴዎፍሎስ በ1963 ዓ.ም ለከፈተኛ ት/ት ወደ ግሪክ ልከዋቸዋል።

ትምህርት በባህር ማዶ

በሕጻንነታቸው ት/ት ፍለጋ ከቤተሰቦቻቸው ተለይተው ከተወለዱበት መንደር ርቀው መሄድ፣ ከክፍለ ሃገር ክፍለ ሃገር መዘዋወር የለመዱት ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ አገር አቋርጠው ባህር ተሻግረው ወደ ግሪክ በመሄድ በተለያዩ  ኮሌጆች እየተዘዋወሩ ለቤ/ክናቸውና ለሃገራቸው የሚጠቅም ከፍተኛ እውቀት ገብይተዋል። ብጹዕነታቸው በግሪክ ቆይታቸው፦
  • በደሴተ ፍጥሞ ለሁለት ዓመታት መንፈሳዊ ት/ት ተምረው ዲፕሎማ፣
  • በአቴንስ ዩኒቨርስቲ ለአራት ዓመታት የስነ መለኮት ት/ት ተምረው ማስትሬት ዲግሪ፣
  • በሲውዘርላንድ ፍሪበሪን ዩኒቨርስቲ የፈረንሳይኛ ቋንቋ አጥንተው የምስክር ወረቀት፣
  • በኢየሩሳሌም ደብረ ጽዮን የግሪክ መንፈሳዊ ኮሌጅ የአረቢኛ ቋንቋ አጥንተው የምስክር ወረቀት አግኝተዋል።

የብጹዕ አባታችን አገልግሎት መጀመር

ከዚያም በኢየሩሳሌም በሚገኙት የኢትዮጵያ ገዳማት በተለይም በደብረ ገነት ኪዳነ ምህረት የኢትዮጵያውያንን ልጆች በማሰባሰብ ኢትዮጵያዊ ባህላቸውንና ቋንቋቸውን ያስተምሩ ነበር። ከዚያም በተጨማሪ ለገዳሙ የገቢ ምንጭ እንዲሆን የዕጣንና የከርቤ ቅመማ ያካሂዱ ነበር። እግዚአብሔር በየትኛውም ቦታ እና ጊዜ ሰወች አሉት። ሰወች ቤ/ክን ለመጣል ሲነሱ እግዚአብሔር ደግሞ  ሊያነሳት የራሱን ሰወች ያስነሳል። ቤ/ክ በወቅቱ ሥልጣን በያዘው ጊዜያዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ ተጽዕኖ  የከፋ ችግር ላይ በወደቀችበት ጊዜ በደሙ የመሰረታት ኢየሱስ ክርስቶስ የእርሱ የሆኑ ሰወች አምጥቶ ሰጥቷታል። ከነዚህም ውስጥ ብጹዕነታቸው አንዱ ናቸው። ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ካልዕ ቤ/ክ በተቸገረችበት ጊዜ ያገኘቻቸው፣ “እግዚአብሔር የቤ/ክ ጠላቶችን ያሳፍር ዘንድ ለተዋህዶ ሃይማኖታችን ጠበቃ አድርጎ  ያስነሳቸው ምሁር አባት ነበሩ።”  ቤ/ክ አስተዳደሯ ተቀልብሶ  ተቸግራ ልጆቿን ስትጠራ በፈቃደ እግዚአብሔር ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስም ከባህር ማዶ ቅድስት ሃገር ከኢየሩሳሌም ተጠርተው መጡ። ብጹዕነታቸው ስለአመጣጣቸው ሲገልጹ፦ “አንድ ቀን ሌሊት ከተኛሁበት ክፍል ውስጥ አንድ ሰው ስሜን ጠርቶ  ይቀሰቅሰኛል። ስነቃም ከራስጌ በኩል አንድ ቀላ ያለ ረጅም ሰው ቆሟል፤ ክፍሉም በነጭ ደመና የተሞላ ነበርና እጅግ በድንጋጤ ላይ እንዳለሁ ሰውየው “ተነሳ ወደ ኢትዮጵያ እንሂድ” ይለኛል። ለምን? በማለት ስጠይቀው ወንጌል እናስተምራለን። አሁን ከዚህ የምትቀመጥበት ጊዜ አይደለምና ተነሳ እንሂድ  ይለኛል። በጥያቄው እና በትዕዛዙ ግራ በመጋባት አንተ ማነህ? ብዬ ስጠይቀው “ኤፍሬም ሶሪያዊ ነኝ” ብሎኝ ተሰወረብኝ። የሆነውን ነገር ማሰላሰል ጀመርኩ። በእንዲህ ሁኔታ ሌሊቱ አልፎ ንጋቱ ተተካ በበነጋውም ጥሪ ይደርሰኛል። ጥሪውም ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ  ቤ/ክ መንበረ ፓትሪያርክ ከብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዘንድ ነበር። ብለዋል። በዚህ ሁኔታ ወደ አ/አ የመጡት ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ልዩ ልዩ መንፈሳዊ አገልግሎት ማበርከት ጀመሩ። በጥር 13 ቀን 1971 ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የአስራ ሶስት ኤጲስ ቆጶሳት ሥርዓተ ሲመት ተፈጽሟል። ቤ/ክ በአንድ ጊዜ 13 ኤጲስ ቆጶሳት ስትሾም የመጀመሪያዋ ነው። በዕለቱ አባ መዝገበ ሥላሴ ክፍሌም ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ካልዕ የሸዋ ሃገረ ስብከት ኤጲስ ቆጶስ ተብለው ተሹመዋል።

በኢትዮጵያ ቤ/ክ “ጎርጎሪዮስ” በሚል ስያሜ የተጠሩት አራቱ ሊቃነ ጳጳሳት፦
  • ነሐሴ 25 ቀን 1952 ዓ.ም የተሾሙት አቡነ ጎርጎሪዎስ ቀዳማይ የከፋ ሊቀ ጳጳስ
  • ጥር 13 ቀን 1971 ዓ.ም የተሾሙት ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ካልዓይ የሸዋ ሊቀ ጳጳስ
  • ጥር 18 ቀን 1983 የተሾሙት ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ሣልሳይ
  • ኅዳር 4 ቀን 1987 ዓ.ም የተሾሙት ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ራብዓይ የምስራቅ ሸዋ ሊቀ ጳጳስ ናቸው።

የጵጵስናና የዝዋይ ካህናት ማሰልጠኛ  አገልግሎት

ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ካልዕ ለጵጵስና ሲመረጡ የጠበቃቸው እጅግ ከባድ ኃላፊነትና መሥዋዕትነትን የሚጠይቅ ፈተና ነበር። ደርግ አርቆ  አስተዋይ፣ ቆራጥና ፍጹም መንፈሳዊ አባቶችን በኃይል አስወግዶ ቤ/ክንን ባዶ ሊያደርጋት ሲያስብ እግዚአብሔር ባወቀው የቀደሙትን አባቶች አሠረፍኖት የሚከተሉ አርቆ  አስተዋይ፣ ቆራጥና ፍጹም መንፈሳዊ አባት ተተኩ። ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ዛሬ በአራት አህጉረ ስብከት ተከፍሎ  በአራት ሊቃነ ጳጳሳት የሚተዳደረውን የሸዋ ሃገረ ስብከት በአንድ ላይ ይዘው ከየካቲት ወር 1971 ዓ.ም ጀምሮ መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን ጀምረዋል። ብጹዕነታቸው የቅዱስ ፓትሪያርኩ እንደራሴ እና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ሆነው በመሾማቸው ከሃገረ ስብከታቸው ጋር ተደራራቢ ኃላፊነትን ተሸክመዋል። ብጹዕነታቸው በእርሻ ውስጥ ልብሳቸውን እንቧይ እየቧጠጠው እሾህ እየቀደደው ከተማሪዎች ጋር ይጓዙ ነበር። በስራ ጊዜ መንገድ አይመርጡም። አትክልቱን ዘወትር ጠዋት እና ማታ ይጎበኙት ነበር። ኮርሰኞች ጠዋት ከእንቅልፋቸው ሲነሱ ብጹዕነታቸውን የሚያገኙዋቸው በአትክልቱ ውስጥ ነበር።  ብጹዕነታቸው ብዙ ጊዜ ከአትክልት ውስጥ ስለማይጠፉ በወባ ተይዘው ክፉኛ በመታመማቸው ለህክምና ወደ አ/አ ሔደው ነበር። ህክምና አግኝተው ሲሻላቸው ብጹዕ አቡነ ተ/ሃይማኖት “ከአሁን በኃላ ወደ ዘዋይ አይሂዱ። ለማሰልጠኛው ጥሩ አባት ሰይመው፣ አ/አ ተቀምጠው በስልክ መመሪያ እየሰጡ የከታተሉ” ብለዋቸው ነበር። ብጹዕነታቸው ግን “የምሞተው እዚያው በልጆቼ መካከል ነው። ለወባ ብዬ ክርስቶስ ያሸከመኝን መስቀል ጥዬ ልጆቼን በትኜ አ/አ አልቀመጥም” በማለት ወደ ዘዋይ ተመልሰዋል። ብጹዕነታቸው በየጢሻው የለበሱትን ልብስ ለብሰው ሲሔዱ ጋሬጣ እንኳን ሲይዘው መለስ ብለው አያዩትም ነበር። “ትርጉሙ ምን እንደሆነ ባይገባኝም ዘወትር ትዝ የሚለኝ ነገር ልብሴን እንጨት ይዞታል ብለው እንኳን ዘወር ብለው አለማየታቸው ነው። ብቻ ወደፊት ለሥራ መሄድ እንጂ ልብሴ ይቀደዳል፣ ይበላሻል በሚል ስጋት ወደኋላ የሚሸሹ አባት አልነበሩም። ብጹዕነታቸው ልብሳቸው ቢቀደድ ቢተረተር እንዴት ይህን ለብሼ እታያለሁ ብለው የሚጨነቁ ሳይሆኑእንደ ትጉኅ ገበሬ ተራ ልብስ፣ የተሸታተፈ ቀሚስ ለብሰው ነጠላቸውን አደግድገው ታጥቀው በመካከላችን የሚገኙ አባት ነበሩ”። ብጹዕነታቸው በቤ/ክ፣ በአደባባይ ዘወትር የማይለዋወጥ አቋቋም ነበራቸው። በትረ ሙሴያቸውን በቀኝ ክርናቸው ተደግፈው፣ በግራ እጃቸው የበትረ ሙሴውን ጫፍ ይዘው መስቀላቸውን በቀኝ እጃቸው ይዘው ጫፉን ጉንጫቸው ላይ አሳርፈው ይቆማሉ። ሲቀመጡም በፍጹም እግራቸውን አዛንፈው ወይም አነባብረው አይቀመጡም። እግርን ማዛነፍ እና ማነባበር በእርሳቸው ዘንድ ታላቅ ኃጢያት ነው። ይህ በራሱ የጸሎት የጸሎት ሥርዓት ነውና ። ብጹዕ አባታችን ለተማሪዎች ከፍተኛ ፍቅር የነበራቸው አባት ነበሩ። ከኢትዮጵያ ውጪ ሔደው ሲመለሱ ከቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባም ሲወጡ ቀኑ በጣም መሽቶ ዝዋይ ገብቶ  ለማደር አስቸጋሪ ካልሆነ በስተቀር አዲስ አበባ ማረፍ አይፈልጉም። ለምን አ/አ ትንሽ ቀናት አያርፉም? ተብለው ሲጠየቁ “ ከልጆቼ ስለይ እሳሳለሁ” ይላሉ። ዝዋይ ሲገቡም ቤ/ክ ተሳልመው ወደቤት ገብቼ ትንሽ ልረፍ፣ ልብሴን ልቀይር ሳይሉ በቀጥታ ወደ ክፍል ገብተው ተማሪዎቹን ያዩ ነበር። ማታ ከሰርክ ጸሎት በኃላ ደግሞ  ከዘዋይ የሄዱበትን ምክኒያት ያጋጠማቸውን ሁኔታ እና ተማሪዎቹ ሊያውቁ የሚገባቸውን ነገሮች ይገልጹላቸው ነበር። ብጹዕነታቸው ከተማሪዎቻቸው መለየት ስለማይሆንላቸው የሚመገቡትም ከተማሪዎች ጋር በአንድነት የምግብ አዳራሽ ውስጥ ነበር። ከተማሪዎቹ የሚለዩት በሚቀመጡበት ጠረጴዛ ብቻ ሲሆን የሚመገቡት ለተማሪዎቹ የተዘጋጀውን ምግብ፣ የሚጠጡት በበርሜል የተፈላውን ሻይ እንጂ የተለየ ነገር አይዘጋጅላቸውም ነበር። ብጹዕነታቸው የላመ የጣመ የሚመገቡ፣ ይህ ያስፈልገኛል፣ ይህ ይዘጋጅልኝ በማለት የሚጠይቁ አባት አልነበሩም። ሰውነታቸው የገዘፈው በጸጋ እግዚአብሔር እንጂ በምግብ አልነበረም። በመጨረሻ አካባቢ ብጹዕነታቸው በብርድ በመታመማቸው በምግብ አዳራሽ ተቀምጠው መመገብ ቢያቆሙም ከቤታቸው ሄዶ  የሚመገቡት ያንኑ ለተማሪዎች የተዘጋጀውን ምግብ ነበር። መነኮሳት የምግብ አዳራሽ ውስጥ በሚገኘው  አንድ ክፍል ተቀምጠው ሲመገቡ መጽሐፈ መነኮሳት እየተነበበላቸው ሥርዓተ አበውን ይማሩ ነበር። ስለዚህ በምግብ አዳራሽ ውስጥ ምንም አይነት ድምጽ ማሰማት አይፈቀድም። ሲመገብ ወጥ ያነሰው፣ ውሃ የፈለገ ቢኖር እጁን አንስቶ  መጋቢውን ወይም አሳላፊውን በጥቅሻ ጠርቶ  ያስጨምራል እንጂ ድምጽን አሰምቶ መጣራት፣ ማውራት አይፈቀድም። ተመጋቢዎች በፍጹም ወጥ ማስተረፍ አይፈቀድላቸውም፣ በሳህን ላይ ያወጣውን ወጥ የመጨረስ ግዴታ ነበር። ብጹዕነታቸው ለተማሪዎች የስነ ምግባር ት/ት ከፍተኛ ትኩረት ይሰጡ ነበር። የገዳሙ ተማሪዎች ሁሉ ለገዳሙ ሕግና ስርዓት ተገዥ መሆን ይጠበቅባቸዋል። ሕግ ተላልፎ፣ ሥርዓት ጥሶ የተገኘ ተማሪ ጥብቅ የሥነ ስርዓት እርምጃ ይወሰድበታል። ብጹዕነታቸው በብልሹ ተማሪዎች ላይ የማያዳግም ውሳኔ በመስጠት ልጆችን በሥርዓት ማሳደግ እንጂ ጥፋትን ሸፋፍኖና አለባብሶ  ማለፍ አይወዱም። ውሳኔያቸው የግል ጥቅሜን ያስቀርብኛል፣ ክብሬን ይጋፋኛል ከሚል ስጋት የመነጨ ሳይሆን ልጆቼን ያበላሽብኛል ብለው ስለሚፈሩ፣ እንዲሁም የተጀመረው ዓላማ እንዳይጨናገፍ ስለሚፈልጉ ነው  እንጂ ሰወችን ለማሳዘን፣ ለመጉዳትና ለመግፋት ፍላጎት ኖሯቸው አይደለም። ብጹዕነታቸው ፈጽሞ ሰወችን ማጉላላና ደጅ ማስጠናት አይሹም። ለማንም የሚገባውን አይከለክሉትም፣ የማይገባው ከሆነ ደግሞ  ሌላ ዕድል ሞክር በማለት ቁርጥ ያለና ግልጽ ውሳኔ ይወስናሉ። አንድ ጊዜ ለኮርስ ከመጡ ተማሪዎች መካከል አንዱ በማሰልጠኛው የሚሰጠውን ት/ት የማጠቃለያ ፈተና ሲወስድ ውጤቱ ለምረቃ ሊያበቃው አልቻለም። ሌላው ቀርቶ ንባብ እንኳን አያውቅም ነበር። ስለዚህ ብጹዕነታቸው እንደገና እንዲማር ይወስናሉ። ይህንን የሰሙ ብዙ ሰወች በሽምግልና መጥተው ምንም የማያውቀው ተማሪ እንዲመረቅ ይለምኑአቸዋል። ብጹዕነታቸው ግን “ተማሪውን ለማሳዘን ፈልጌ ሳይሆን ምንም ነገር የማያውቅ ሰው መርቆ  መላክ በቤ/ክ አገልግሎትና በራሱ በሰው ህይወት መቀለድ ነው።” በማለት ልጁ ዳግመኛ እንዲማር አድርገዋል። ለዚህም ብጹዕነታቸው ብዙ ጊዜ “እዚህ በረሃ የወደቅኩት ሰው አፈራ በማለት እንጂ አልጫ ፍትፍት ብፈልግ ኖሮ መሃል ከተማ አልወጣም ነበር?” በማለት ሃሳባቸውን ያስረዱ ነበር። ብጹዕነታቸው ከገዳሙ ጀርባ ቦጨሳ ከሚባለው መንደር ብዙ ልጆችን ተቀብለው አሳድገዋል፤ አስተምረውም ለቁም ነገር አብቅተዋል። ሌሎች ደግሞ ምግብ እየተመገቡ፣ አልባሳት እየተሰጣቸው በተመላላሽነት ያድጉ ነበር። እነዚህ ልጆች አንድ ቀን ማታ ከገዳሙ ዕቃ ሰርቀው ይወጣሉ። በዚያ ድቅድቅ ጨለማ የገዳሙ ተማሪዎች በየአቅጣጫው ልጆቹን ፍለጋ ተሯሩጠው ይይዙዋቸዋል። ከሰረቁት ዕቃ ጋርም ወደ ገዳሙ አምጥተው ለብጹዕነታቸው ያስረክባሉ። ጠዋት በግቢ ውስጥ ያሉት ሰወች ተጠርተው ይሰበሰባሉ።ብጹዕነታቸው ልጆቹን “ይህ ቤት የምትበሉበት፣ የምትጠጡበትና የምትለብሱበት አይደለም? ለምን ይህን አደረጋችሁ?” በማለት ጠየቋቸው እና መጋቢውን ጠርተው ዕቃውን ተረክበው ልጆቹን በነጻ ወደቤታቸው እንዲያሰናብቷቸው ይወስናሉ። የያዝዋቸው ተማሪዎች ግን የብጹዕነታቸውን ውሳኔ ሲሰሙ ተናደዱ። ያን ያህል ሮጠውና ደክመው ሌቦቹን ከያዙ በኋላ ወደ ፖሊስ ጣቢያ መሄድ ሲገባቸው በነጻ በመለቀቃቸው ይከፋሉ። ሌቦቹ ከተለቀቁ በኋላ ብጹዕነታቸው “ልጆቹ በመለቀቃቸው ማዘን የለባችሁም። በእርግጥ ልጆቹን ፖሊስ ጣቢያ ወስደን ማሳሰር እንችል ነበር። ነገር ግን  ፖሊስ ዘንድ ተካሰን ስንቀርብ ኦርቶዶክሶች ተሰራርቀው፣ ተካሰው ቀረቡ እንባላለን። እራሳችንን ለጠላት መሳለቂያ እናደርጋለን። በሌላ በኩል ልጆቹን አሳልፈን የምንሰጠው ፈሪሃ እግዚአብሔር ለሌላቸው ፈራጆች በመሆኑ በጣም ሊሰቃዩ እና ሊጎዱ ይችላሉ። ልጆቼ የእናንተ ፊት እና የእናንተ ዓይን እራሱ ታላቅ ዳኛ ነው። ከፊታችን በመቆማቸው የተቀጡት ቅጣት በጣም ከባድ ነው” በማለት ተማሪዎቹን አሰናበቱ። ልጆቹ ባይሰርቁ ኖሮ እንዲህ  አይነቱን ት/ት ለምንግዜውም አያገኙትም ነበርና ብዙ ተማሪዎች በድርጊቱ እግዚአብሔርን አመሰገኑ። ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ተማሪዎቻቸውን “ለትምህርት ጊዜ አትስጡ የምንኖረው በፖለቲካ ዓለም ውስጥ ነው። ገማቾች ጥያቄ ያቀርቡብናል። ያን ሁሉ ካልተቋቋምን እግዚአብሔር አይደሰትብንም። በመማር ብቁ እንሁን”  በማለት በሁለት ወገን የተሳለ  ሰይፍ እንዲሆኑ ያበረታቷቸው ነበር። የቅኔ ተማሪዎችን፣ የዜማ ተማሪዎችን በሥራ እያወዳደሩ ሽልማት ይሰጡዋቸው ነበር። ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ተማሪዎችን አስተምሮና መርቆ  ማሰናበት ብቻ ሳይሆን ከምረቃም በኋላ የተማሪዎችን ሕይወት በሚገባ የሚከታተሉ አባት ነበሩ። ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ ከብጹዕነታቸው ጋር እንዴት መገናኘት እንዳለባቸው ያጋጠማቸውን ችግር፣ የሥራ ፍሬ (ምን ያህል ኢአማንያንን እንዳጠመቁ፣ ያጋጠማቸውን የመናፍቃን እንቅስቃሴና መሰናክል) በጽሁፍ አዘጋጅተው ወደ መንበረ ጵጵስናቸው (ዝዋይ ገዳም) እንዲያመጡ ምክር ይሰጡ ነበር። ከከፍተኛ ት/ት ተቋማት በክረምት ወራት መጥተው የሚማሩ ተማሪዎችን እንቅስቃሴም እንዲሁ በየክረምቱ አንድ ትልቅ መንፈሳዊ የውይይት መርሐ ግብር አዘጋጅተው እንዴት እንዳስተማሩ፣ ያጋጠማቸውን ችግር እያነሱ ከተወያዩ  በኋላ ያለፈው ስርዓት ለሃይማኖት አስቸጋሪ ስለነበር በብልሃት በመንፈሳዊ ጥበብ እንዴት መመላለስ እንዳለባቸው ይመክሯቸው ነበር። ዓመቱ ደርሶ ተማሪዎች ተመልሰው እስኪመጡ ድረስ በደብዳቤ እየተጻጻፉ መመሪያ ይሰጡዋቸው ነበር። ብጹዕነታቸው በአባትነታቸው የሚጠበቅባቸውን ሁሉ ለተማሪዎቻቸው አድርገዋል።

ብጹዕ አባታችን በዓለም ዙርያ

ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ካልዕ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ  ቤ/ክ ታላቅነትና ማንነት በዓለም ያሳወቁ የቤ/ክ መልዕክተኛ ነበሩ። ብጹዕ አባታችን ከአምስት በላይ የተለያዩ  ቋንቋዎች ተሰጥኦና ልዩ ልዩ  የንግግር ጸጋ፣ ሰብኮ የማሳመንና ተናግሮ  የማሳሰብ ሃብት ስለነበራቸው ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው በተለያዩ  ዓለም አቀፋዊ ጉባኤዎች የኢትዮጵያን ቤ/ክ ወክለው እንዲገኙ በወሰነው መሰረት፦

  • ግንቦት 7 ቀን 1972 ዓ.ም በግብጽ ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ላይ በደረሰው ችግርና ፈተና የኢትዮጵያ ቤ/ክ ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰማውን ጥልቅ ሃዘንና የቅዱስ ፓትሪያርኩን መልዕክት እንዲያደርሱ ተልከዋል።
  • ሚያዝያ 20 ቀን 1973 ዓ.ም በሩማንያ በተዘጋጀው የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ጉባኤ ላይ የኢትዮጵያን ቤ/ክ ወክለው ተገኝተዋል።
  • ከመስከረም 27 እስከ ጥቅምት 10 1974 ዓ.ም በምዕራብ አውሮፓ በጀርመንና በኦስትርያ በብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ተ/ሃይማኖት መሪነት  በተደረገው ጉብኝት ከተጓዘው ልዑካን መካከል አንዱ ነበሩ።
  • ታህሳስ 1 ቀን 1978 ዓ.ም በጄኔቫ ላይ በተደረገው የመላው ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ስብሰባ ላይም የኢትዮጵያን ቤ/ክ ወክለው ተሳትፈዋል።
  • ግንቦት 26 ቀን 1979 ዓ.ም በለንደን ከተማ ባለችው የኢትዮጵያ ቤ/ክ የተከሰተውን ችግር ለማጥናት እና ለመፍታት በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ እንዲሔዱ ተደርጎ ብጹዕነታቸው የአጥቢያ ቤ/ክኒቱ የምትጠናከርበትና የምታድግበትን ሁኔታ ከቅዱስ ሲኖዶስ ደንብና መመሪያ ጋር በማጣጣም ለችግሩ መፍትሔ ሰጥተዋል።
  • ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ በዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት የእምነትና የሥርዓት ጉባኤ ቋሚ አባል ሰለነበሩ ከነሐሴ 1 ቀን እስከ ከነሐሴ 15 ቀን 1981 ዓ.ም በጉባኤው ተካፋይ ሆነዋል።
  • ሐምሌ 16 ቀን 1979 ዕም በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ መሰረት በፓሪስ በተደረገው ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ጥናት ላይ ተገኝተው በእንግሊዘኛ ቋንቋ “የኢትዮጵያ ቤ/ክ ማህበራዊ አገልግሎት ትላንትናና ዛሬ” በሚል ጥናታዊ ጽሁፍ አዘጋጅተው አቅርበዋል።
  • ከጥቅምት 13 ቀን 1984 ዓ.ም(እኤአ) በኤች ሚዚን በተካሄደው የምስራቅ ኦርቶክስ ተዋህዶ አብያተ ክርስቲያናት ጉባኤ ተሳታፊ ሆነዋል።
  • ሐምሌ 6 ቀን 1990 ዓ.ም ለአለም አብያተ ክርስቲያናት 7ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ለተደረገው አህጉራዊ ዝግጅት ወደ ጋና ተጉዘው ስብሰባውን ተካፍለዋል።
  • ሞስኮ ውስጥ ዓለም ከኒውክሊየር ስጋት ነጻ እንድትሆን፣ የሰው ዘር ከእልቂት እንዲተርፍ በጦር መሳሪያው ምርት ላይ ማዕቀብ ለመጣል በተካሄደው ዓለም አቀፋዊ ስብሰባ ላይ ተካፋይ ሆነዋል።
  • በ1979 ዓ.ም በለንደን ከተማ ለምትገኘው ቅድስት ማርያም ቤ/ክ ጃማይካውያን ዲያቆናትን እንዲያሰለጥኑ በቅዱስ ሲኖዶስ በታዘዙት መሰረት በዝዋይ ካህናት ማሰልጠኛ በእንግሊዘኛ ቋንቋ የኢትዮጵያ ቤ/ክንን ታሪክ እምነትና ትውፊት አስተምረው በብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ተ/ሃይማኖት አንብሮተ ዕድ ማዕረገ ቅስና እንዲቀበሉ አድርገዋል። ብጹዕ አባታችን ወደተለያዩ የውጭ ሃገራት ለስብሰባ ሲሄዱ በሚሰጣቸው የጉዞ አበል ለራሳቸው የሚሆኑ በርካታ ነገሮችን ይዘው መምጣት ሲችሉ የሚያስጨንቃቸው የቤ/ክና የልጆቻቸው ነገር ብቻ በመሆኑ ከቦስተን የብረት ድስት ገዝተውተሸክመው መምጣታቸውን በተጨማሪም የተለያዩ ምዕመናንን በማስተባበር፣ ከውጭ ሃገር ዕርዳታ በማሰባሰብ ለገዳሙ ተማሪዎች አልባሳት እና መመገቢያ ዕቃዎችን አሰባስበዋል።

የብጹዕ አባታችን የግል ጠባይ

ብጹዕ አባታችን በደስታ የመፈንደቅ በኅዘን የመቆራመድ ጠባይ የላቸውም። በሚሄዱበት ቦታ ሁሉ ብዙ ህዝብ ሲቀበላቸው ተሰብስቦ ሲመጣ በማየታቸው ኩራት አይሰማቸውም። ራሳቸውን የገዙ በዓላማ የሚጓዙ ጽኑዕ አባት ነበሩ። ብጹዕነታቸው በደስታ የሚፈነጥዙ አባት ስላልነበሩ ሰወች በዚህን ጊዜ ተደሰቱ በዚህን ጊዜ ተከፉ ብለው በቀላሉ መናገር አይችሉም ነበር።  ብጹዕነታቸው በጣም ጨዋታ አዋቂ ናቸው።  እንግዶች ሲመጡ “የቀድሞ  አባቶች እንዲህ ያደርጉ ነበር፣ እንዲህ ይሉ ነበር።” የሚሉ ወጎችን እያነሱ ሲጫወቱ መጠነኛ ፈገግታ ይታይባቸዋል እንጂ ብዙም አይስቁም ነበር። ዘወትር ተመሳሳይ አባታዊ ገጽታ ይታይባቸው ነበር እንጂ ደስታቸውም ሃዘናቸውም አይታወቅም። ነገር ግን ብጹዕነታቸው በገዳሙ የሚገኙትን ሕጻናትና ተማሪዎች በማግኘታቸው ደስትኛ እንደሆኑ ሲናገሩ ይደመጡ ነበር። ብጹዕ አባታችን ጠላት በዝቶብን፣ ወራሪ ተነስቶብን የሚገባንን ያህል ባለመንቀሳቀሳችን በጣም ያዝኑ እንደነበር ለተማሪዎቻቸው ነግረዋቸዋል። ብጹዕነታቸው  የቤ/ክ ጉዞ  በዓለም ላይ እንዴት እንደነበረ፣ በውስጥ በአፍዓ የነበረውን ሕይወት በጥልቀት ያውቁ ስለነበር በቤ/ክ ውስጥ የጎደለው ነገር የሚሟላው መቼ  ነው በማለት፤ ቤ/ክ ሐዋርያዊት እና ጥንታዊት እንደመሆኗ ክብሯ በዓለም ዙሪያ እንዲታወቅ፣ የእግዚአብሔር መንግስት ወንጌል በዓለም እንዲሰበክ ከነበራቸው ከፍተኛ ጉጉት የተነሳ እንደ ዮሐንስ ፍቁረ  እግዚእ በህይወት ዘመናቸው ሙሉ ስለ ቤ/ክ ያዝኑ ነበር። ብጹዕነታቸው ተማሪዎች እንዳሰቡት ትምህርታቸውን  ሳይቀበሉ ሲቀሩ ሥርዓተ ቤ/ክ ሲጣስ እንዲሁም ቤ/ክ በቂ አገልግሎት፣ የተዋጣ አመራር የምታገኘው መቼ ነው? እንደቀድሞው በዓለም ዙሪያ ሰፍታ የምትታየው መቼ ነው? እያሉ ዘወትር ያዝኑ ነበር። ብጹዕነታቸው ወደ ውጭ ሃገር ለስብሰባ ሄደው ሲመለሱ በሃይማኖት የማይመስሉን ሰወች በጉልበት የዘረፉንን፣ በስርቆሽ የወሰዱብንን የብራና መጽሐፍት፣ የወርቅና የብር መስቀሎች፣ የተለያዩ አክሊላትና የነገስታት ዘውዶች፣ ቅዱሳት ስዕላትና ታቦታት የራሳቸው እንደሆነ አድርገው በቤተመዘክራቸው አስቀምጠው በታሪካችን ሲነግዱበትና እኛን ሲያስጎበኙን ማየታቸው በጣም አሳዝኖአቸው ይህን ስሜታቸውን በት/ታቸው ገልጠውት ነበር። የብጹዕነታቸው የዘወትር ሃዘን በቤ/ክ ጉዳይ እንጂ በግል ሕይወታቸው “ይህ ቀረብኝ፣ ይኽኛው አነሰኝ፣ አልተመቸኝም ” ከሚል ሃሳብ የመነጨ አልነበረም። ብዙ ጊዜ የሚያውቋቸው ሰወች ብጹዕነታቸው በቤ/ክ በመጣ ነገር፣ በስርዓት መጣስ ሲበሳጩ በቀኝ እጃቸው በያዙት መስቀል የግራ እጃቸውን መዳፍ መታ መታ ያደርጋሉ።” በማለት አልፎ  አልፎ  ስሜታቸውን መረዳት እንደሚችሉ ይናገራሉ። አንዳንዶች ደግሞ ብጹዕነታቸው “ኃይለኛ ቁጠኛና ጨካኝ” እንደነበሩ የገልጻሉ። በዘመናችን በመቶዎች የሚቆጠሩ ልጆችንና ተማሪዎችን ጠባይዕ ማረቅ አቅቷቸው የሚማረሩ፣ በንዴት ተገቢ ያልሆነ ቅጣት የሚቀጡ ወላጆች ቁጥር ምን ያህል እንደሆነ ቤት ይቁጠረው! ልጆችን በአግባብ፣ በሥርዓት ማሳደግ በጣም ከፍተኛ ኃላፊነት ይጠይቃል። ብጹዕነታቸው በገዳሙ የሚገኙትን ህጻናት፣ መደበኛ ተማሪዎች እና ኮርሰኞች ተቆጣጥረው ከመያዛቸው ባሻገር ዛሬ በአራት ሊቃነ ጳጳሳት የሚተዳደረውን የሸዋን ሃገረ ስብከት መንፈሳዊ አገልግሎትና አስተዳደር ይዘው የሚጠበቅባቸውን ሐዋርያዊ ግዴታ እየተወጡ ነበር። ታዲያ በዚህ እጅግ ከባድ ሃላፊነት ውስጥ ሆነው በተወሰነ ዓላማ እንዲጓዝ፣ በሥርዓት እንዲመራ ብዙ ደክመው፣ መክረው ያሳደጉት ተማሪ ድካማቸውንና ልፋታቸውን ሁሉ ገደል ሰዶ በማይሆን ቦታ ሲያገኙት በአባትነታቸው ቢቆጡት፣ ቢቆነጥጡት ምን ክፋት አለው? ቅጣታቸውስ አግባብ አይሆን ይሆን? ልጁን የማይቀጣስ ይኖር ይሆን? አንዳንዶች ብጹዕነታቸው ሰው መሆናቸውን ፈጽመው ሳይዘነጉት አልቀሩም። ብጹዕነታቸው ያ ሁሉ ድካም፣ ልፋት “ነገ ሰው አገኛለሁ” በሚል ተስፋ በዚያ በረሃ መንገላታታቸው፣ ልጆችን ለመመገብ በሰው አይን መገረፍ ውጤት አልባ ሲሆን መቆጣታቸው፣ መበሳጨታቸው ከሰው የተለየ ተፈጥሮ ኖሮዋቸው ይሆን? ጌታም በቤተ መቅደስ የማይገባ ነገር ሲፈጸም በዝምታ አልተመለከተም። ጅራፉን አንሥቶ  ሥርዓት አልበኞችን እየገረፈ አስወጥቷል። ደቀ መዛሙርቱም የማይገባ ነገር ሲፈጽሙ ተቆጥቷቸዋል። የብጹዕ አባታችንን ሕይወት ቀረብ ብሎ ለተመለከተ፣ ታሪካቸውን ላጠና ሰው በጣም ሩኅሩኅ፣ ለሰው አዛኝ፣ ሰለሰው ራሳቸውን መስዋዕት አድርገው የሚያቀርቡ አባት እንደሆኑ ያስረዳል። ውሳኔያቸው ሁሉ በገዳሙ የሚገኙት ልጆች እንዳይበላሹ ከመስጋት፣ የልጆቹን ደህንነት ከመጠበቅ አንጻር እንደሆነ ይገነዘባል።
 
ብጹዕ አባታችን ለፍሬ ያበቋቸው ጳጳሳት

የብጹዕነታቸውን ት/ትና ምክር ሰምተው፣ የዓለምን ደስታ ንቀው ንጽህናንና ድንግልናን ገንዘብ ያደረጉ ወጣቶች በርካታ ናቸው። ብጹዕነታቸውን በእግር ሳይሆን በገቢር ተከትለው ከአጥቢያ ቤ/ክ አስተዳዳሪነት እስከ ሊቀ ጵጵስና የደረሱ ብዙ ደቀ መዛሙርትን አፍርተዋል። ለአብነትም፦
  • ብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ራብዕ የምስራቅ ሸዋ ሃገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
  • በቅርቡ ያረፉት ብጹዕ አቡነ መልኬጼዴቅ ካልዕ የከምባታ ሐድያና ጉራጌ ሃገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
  • ብጹዕ አቡነ ኤልያስ ሣልስ የወለጋ ሃገረ ስብከት ጳጳስ እና ሌሎችም
የብጹዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ የዝዋይ ፍሬዎች ናቸው።

ብጹዕ አባታችን ለወጣቱ

ወጣቱ ወደ ቤ/ክ እንዴት መቅረብ፣ ማስተማር ማገልገል እንደሚችል እያሰቡ የተለያዩ ዘዴዎችን በመቀየስ፣ ለወጣቱ የሚጠቅም ነገር ለማዘጋጀት ከመጨነቅ፣ “እናንት የሰ/ት/ቤ ተማሪዎች የቤ/ክ የስስት ልጆች፣ የቤ/ክ ችግኞች ናችሁ::” እያሉ ከማበረታታት ሌላ ውዳሴ ከንቱን የሚሹ አባት አልነበሩም:: ውዳሴ ከንቱ ብዙዎችን የሚጥል፣ የሚያደክምና የሚጎዳ ታላቅ ደዌ መሆኑን ስለሚያውቁ ነው።

በ1980 ዓ.ም በምስካየ ኅዙናን መድሃኔአለም ገዳም በተምሮ  ማስተማር ሰ/ት/ቤ ለመጀመሪያ ጊዜ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የምረቃ መርሐ ግብር ሲዘጋጅ ከተገኙት ብጹዓን ሊቃነ ጳጳሳት አንዱ ብጹዕ አባታችን ነበሩ:: በዕለቱ ብጹዕነታቸው “በዚህ ዘመን እግዚአብሔር አምላካችን ብሎ ስመ እግዚአብሔርን ጠርቶ በቤ/ክ መሰብሰብ ሰማዕትነት ነው።” በማለት ሰፊ ት/ት ሰጥተው ነበር። በ1979 ዓ.ም በዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ወደ ዝዋይ ገዳምና ካህናት ማሰልጠኛ ገብተው ለመማር ጠይቀው በጊዜና በሁኔታ አለመመቻቸት ዕድሉን ያላገኙት ተማሪዎች በዕለቱ ጥያቄያቸውን በድጋሚ አነሡ በዚህን ጊዜ ብጹዕነታቸው “እኔ ደስታውን አልችለውም:: የዩኒቨርስቲ ተማሪ ቤ/ክ ልማር ብሎ መጥቶ ነው?! በእርግጥ የማለብሳቸው ልብስ፣ የማበላቸው ጥሩ ምግብ የለኝም:: የማሳርፍበት ቦታም የለኝም:: ግን እዚያ ከማሳድጋቸው ህጻናት የተረፈውንም ቢሆን ንፍሮ ቀቅዬ አበላቸዋለሁ፣ ድንኳን ተክዬም ቢሆን አስተኛቸዋለሁ:: እመጣለሁ ብሎ የሚመጣ ተማሪ ካለ ይምጣ” በማለት መልስ በመስጠታቸው 12 ተማሪዎች ወደ ዝዋይ ገብተው ሊማሩ ችለዋል። በየክረምቱም በህይወተ ስጋ እስከነበሩበት ሐምሌ 1982 ዓ.ም ድረስ በሦስት ጊዜያት 69 የዩኒቨርሲቲና የኮሌጅ ተማሪዎችን በማስተማር ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት አብቅተዋል። ብጹዕ አባታችን ለቤ/ክ ከነበራቸው ታላቅ ፍቅር አኳያ ወጣቶቹን ሰብስበው በሚያስተምሩበት ወቅት ከተለያዩ አቅጣጫዎች ብዙ ፈተና ስለገጠማቸው ወጣቱ ትውልድ ወደ ቤ/ክ ገብቶ ጉልዕ ድርሻ ሲያበረክት እስኪያዩና ያሰቡት እስኪሳካላቸው ድረስ እንቅስቃሴያቸውን ለማንም እንዳይገልጡ ይመክሯቸው ነበር።

ብጹዕ አባታችን የፃፏቸው መጽሐፍት

ብጹዕነታቸው እንደ ቅዱስ ጊዮርጊስ ዘእንዚናዙ ነገረ መለኮትን አብራርተው ባፍ በመጣፍ ያስተማሩ፤ ለነገ የሚጠቅመውን ነገር ሥራ መፍታት በማይወዱት እጆቻቸው ስምንት መጽሐፍትን ያዘጋጁ አባት ነበሩ።

የታተሙ መጽሐፎቻቸው፦
  • መሠረተ እምነት ለሕጻናት፦ ት/ተ ሃይማኖትን ለማስተማር የተዘጋጀ፤
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ታሪክ፦ ከዘመነ ብሉይ እስከ አለንበት ጊዜ ድረስ የተጓዘችበትን ሂደት፣ የቤ/ክኒቱን መሠረት እምነትና ትውፊታዊ ሥርዓት እንዲሁም የኢኮሚኒዝምን መሰረተ ሃሳብ የሚያብራራ፤
  • የቤ/ክ ታሪክ በዓለም መድረክ፦ የቤ/ክ ትርጉምና አመሰራረት ጉዞና መሰናክሎች፣ የተዋህዶ እምነት ከየት መጣ? እና ት/ቱን በሰፊው ያስረዳል።
ሳይታተሙ የቀሩ መጽሐፎቻቸው፦
  • ሥርዓተ ኖሎት
  • ነገረ ሃይማኖት
  • ኦርቶዶክሳዊ የስብከት ዘዴ
  • የሰ/ት/ቤ መመሪያና
  • ቤ/ክህን ዕወቅ የተባሉት ናቸው።

የብጹዕ አባታችን አባባሎች

ብጹዕ አባታችን በተለያዩ ርዕሶች ላይ የተናገሯቸው በርካታ ድንቅ አባባሎች ነበሯቸው።
  • “ስለ እመቤታችን መናገር የምንችለው ስለ ሰው እና ስለ እግዚአብሔር ስናውቅ ብቻ ነው።”
  • “የቤ/ክ ሕይወት በመስቀል ላይ ስለሆነ ፈተና ይበዛበታል። ስለዚህ ከግል ህይወታችሁ ይልቅ የቤ/ክአችሁን አቋም አጠናክሩ።”
  • “ሰው ፍላጎቱን ካላሸነፈ የእግዚአብሔር መሆን አይችልም።”
  • “ሥጋዊ ፍላጎቶችን ማሸነፍ ለአክሊለ ሕይወት የሚያበቃ ሰማዕትነት ነው።”
  • “ኢትዮጵያ ለእግዚአብሔር የምስጢር ሃገር ናት” በማለት የተናገሯቸውን መጥቀስ ይቻላል።

የብጹዕ አባታችን ድንገተኛ እረፍት

ሐምሌ 22 ቀን 1982 ጠዋት ለቤ/ክ አስደንጋጭ እና እጅግ አሳዛኝ ዕለት ነበር። ብጹዕ አባታችን በዚሁ ቀን ከጠዋቱ 1:30 በመቂ ደብረ አሚን ቅዱስ ጊዮርጊስና በቅዱስ ሚካኤል ቤ/ክ ለሚገኙ ምዕመናን ት/ተ ወንጌል ለመስጠት ሲሄዱ በድንገተኛ የመኪና አደጋ በተወለዱ በ50 ዓመታቸው። እስከ ኅልፈተ ዓለም ላይነቁ አንቀላፉ። ያ በርቀት የተያዘ ዕቅድ በአጭር ተቋጨ፣ ያ ሁሉ እረፍት የሌለው ሩጫ ተገደበ፣ ያ ብሩዕ ሃሳብ በድንገት ከሰመ። ከብጹዕነታቸው ጋር ለአገልግሎት አብረው የነበሩት ዲያቆን ጳውሎስ በቀለና የመኪናው አሽከርካሪ ዲያቆን ኤፍሬም ዘውዴም በደረሰው አደጋ በለጋ ዕድሜያቸው በመንገድ ላይ አለፉ። ሐምሌ 23 1982 ዓ.ም ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ፣ ብጹዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የአድባራትና የገዳማት አስተዳዳሪዎች ካህናት እና ምዕመናን በተገኙበት በዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቤተ መቅደስ ውስጥ ሥርዓተ ቀብራቸው ተፈጽሟል።

በብጹዕነታቸው ሳይሰሩ የቀሩ ዕቅዶች

  • የካህናት ማሰልጠኛ ቁጥር ከፍ በማድረግ ያሉትንም አቅም ወደ ኮሌጅና ዩኒቨርስቲ ደረጃ ማሳደግና ሥርዓተ ት/ት በማዘጋጀት ከየአህጉረ ስብከቱ የሚመጡትን ካህናት በብቃትና በጥራት ማሰልጠን ሚቻልበትን ሁኔታ ያስቡ ነበር::
  • በዜግነት ኢትዮጵያዊ ሳይሆኑ የኢኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ እምነትና ሥርዓት ተከታይ የሆኑትን የውጭ ዜጎች ነጻ የት/ት ዕድል በመስጠት በዝዋይ ማሰልጠን
  • ወጣቶችን  ከተለያዩ ኮሌጆችና ዩኒቨርስቲዎች በማሰባሰብ ያለምንም ተጨማሪ በጀት አሰልጥነው በማስመረቅ ነገ ቤ/ክንን ያለምንም ክፍያ እንዲያገለግሉ ማዘጋጀት
  • ከዝዋይ ገዳም በቅርብ ርቀት በሚገኘው በደሴተ ገሊላ የሴቶች ገዳም ለመገደም ከፍተኛ ምኞት ነበራቸው
  • ለዝዋይ ገዳምና ለከተማ ነዋሪዎች አገልግሎት የሚሰጥ ዳቦ መጋገሪያ ለመስራት እና የጤና ጣቢያ በገዳሙ ለማቋቋም  
  • ለገዳሙ ሕጻናት፣ ዲያቆናትና መነኮሳት ዘመናዊ ት/ት ቤ/ት ማሰራት
  • ዘመናዊ ት/ት ለተማሩ መነኮሳት የውጭ ሃገር የት/ት ዕድል እንዲያገኙ መርዳት
እና ሌሎችም ቤ/ክንን የሚያሳድጉ ብዙ ዕቅዶች ነበሯቸው።


የአባታችን በረከት ይደርብን!
ዕቅዶቻቸውን የምንፈጽምበትን ሃይልና ጥበቡን ያድለን
ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን


ምንጭ፦ ከተለያዩ የሐመር እና የስምዓ ጽድቅ እትሞች የተውጣጣ
            በሰሜን አሜሪካ የትምህርት እና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል

 


Written By: admin
Date Posted: 8/4/2011
Number of Views: 4324

Return

  
Copyright 2016 by Mahibere Kidusan USA Center  | Terms Of Use | Privacy Statement