View in English alphabet 
 | Sunday, May 5, 2024 ..:: መቅድም ::.. Register  Login
  

እንኳን ለብርሃነ ልደቱ አደረሰዎ!!!

“ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ስምረቱ ለሰብእ”

ልደተ ክርስቶስን ስናከብር ከላይ የተጠቀሰውን የመላእክት መዝሙር እናስታውሳለን:: ቅዱሳን መላእክት ይህን ሰላምና እርቅን የሚያበስር መዝሙር ለመጀመሪያ ጊዜ የተቀኙት ለ5500 ዓመታት ጸንቶ  የቆየው  የጥል እና  የመለያየት ዘመን ተፈጽሞ የእርቅና የአንድነት ዘመን መጀመሩን ለማወጅ ነው:: በአዳም በደል ምክንያት ለዘመናት ተለያይተው የነበሩት የሰው ልጆች እና ቅዱሳን መላእክት በጌታ  ልደት ምክንያት ይህን መዝሙር አብረው ለመዘመር ቻሉ:: ሁላችንም የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ልጆችም በያለንበት ሆነን በዓለ ልደቱን ስናከብር ይህንን መዝሙር በድምቀት እንዘምራለን::

 

ይህን መዝሙር እያሰማን እርቅና ሰላም የተደረገበትን የልደት በዓል ስናከብር በቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከልም የተጀመረውም የእርቅ ሒደት ፍሬ እንዲያፈራ ልናበረክተው የሚገባንን አስተዋጽዖ ሁላችንም ባለን ድርሻ እና ኃላፊነት ልንወጣ ይገባናል:: ሁሉም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቤተሰብ ይህ የመለያየት ግንብ ፈርሶ ወደ ቀደመ ታሪካችን እና ክብራችን እንመለስ ዘንድ፣ ምስጋናችንም በአንድ መንፈስ ወደ አርያም ያርግ ዘንድ ለእርቀ ሰላሙ የምንችለውን አስተዋጽዖ ለማድረግ ዝግጁ መሆን ይጠበቅብናል::

ጌታችን ብርሃነ ልደቱን በገለጸባት በዚያች የተመረጠች ሌሊት ቅዱሳን መላእክት እና የአዳም ልጆች ታርቀው በአንድ መንፈስ አዲስ ምስጋና እንደተቀኙ ሁሉ እኛም በአስተደዳደር የተለያየችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መታወቂያዋ እና ክብሯ ወደ ሆነው ወደ አንድነትዋ እንድትመለስ ተስፋችንን የፍቅር መሠረት በሆነ በልዑል እግዚአብሔር አድርገን፣ ተማኅጽኖአችንን ወደ አርያም ልናሳርግ ይገባል::

ይህ ጥሪ የተወሰኑ ሰዎችን ብቻ የሚመለከት ጥሪ አይደለም:: የቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባል የሆን ክርስቲያን ሁሉ የሚመለከት ጥሪ ነው:: ስለሆነም ሁላችንም የልደቱን በዓል ስናከብር አንድነታችንን እየናፈቅን፣ የእርቅ ሒደቱም እንዲፋጠን እንደተሰጠን ጸጋ መጠን ተሳትፎ እያደረግን ሊሆን ይገባል:: የእርቅ ሂደቱን የሚያስተባብሩትንም አካላት በሚያስፈልጋቸው ሁሉ ልንደግፋቸው ይገባል::

በማይመረመር ረቂቅ ጥበቡ ከእመቤታችን ነፍስ እና ሥጋን ነስቶ ብርሃን ልደቱን የገለጸልን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተልሔም በፍጹም አንድነት እንደዘመሩት መላእክትና እረኞች እኛም በስሙ የተጠራን የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች በአንድነት ሆነን የምንዘምርበት እና የምስጋና መስዋዕት የምናሳርግበትን ጊዜ እንዲያቀርብልን እንመኛለን:: ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳንም የእርቁን ሒደት በትኩረት እየተከታተለ ለተፈጻሚነቱም የሚችለውን ሁሉ በማድረግ ላይ መሆኑን እየገለጽን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከብርሃነ ልደቱ ረድኤት በረከት ይክፈለን እንላለን::

ረድኤተ  እግዚአብሔር አይለየን

በኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያን የሰ/ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል


Written By: admin
Date Posted: 1/6/2012
Number of Views: 2582

Return

  
Copyright 2016 by Mahibere Kidusan USA Center  | Terms Of Use | Privacy Statement