View in English alphabet 
 | Friday, April 26, 2024 ..:: መቅድም ::.. Register  Login
  

ትምህርተ ሃይማኖት ኦርቶዶክሳዊት

ወልድ ዋሕድ /ክፍል ፪/

በሊቀ ካህናት ኃይለሥላሴ ዓለማየሁ ደስታ


እግዚአብሔር ፈጣሪ ነው

ፈጣሪ ስንል የሌለን ወይም ያልነበረን ነገር በሥልጣኑና በከሃሊነቱ ያስገኘ፣ ዓለምን እምሀበአልቦ /ካለመኖር ወደ መኖር/ የፈጠረ ማለታችን ነው። ዓለምን እምሀበአልቦ ያስገኘ፣ በመለኮታዊ  ሥልጣኑ የሚታየውንና የማይታየውን፣ ግዙፉንና ረቂቁን ፍጥረት ሁሉ የፈጠረ እግዚአብሔር ነው።

እግዚአብሔር ዓለምን /ፍጥረቱን/ ለመፍጠር ምክንያት የሆነው መለኮታዊ ሥልጣኑ ብቻ ነው፤ የፍጥረታት ሁሉ አስገኝ እግዚአብሔር በመሆኑም የፍጥረታት ሁሉ ጌታና ባለቤት እግዚአብሔር ነው። እግዚአብሔር ዓለምን ፈጥሮ እንዲሁ አልተወውም፤ በመግቦቱ ይጠብቀዋል፤ ይህን ዓለም ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣ እግዚአብሔር ብቻ በመሆኑና በመለኮታዊ ሥልጣኑ መሳይ ተወዳዳሪ ስለሌለውም እግዚአብሔር አንድ አምላክ ይባላል።
 

እግዚአብሔር ዓለሙን ሲፈጥር፣ ይሁን ብሎ በቃሉ፣ በመለኮታዊ ሥልጣኑና በከሃሊነቱ ፈጠረው እንጂ ፍጥረታትን ለማስገኘት ሌላ አፍአዊ ምክንያት አላስፈለገውም። እንደዚህ ያለ መለኮታዊ ሥልጣን በሰማይም በምድርም ስለሌለ፣ እግዚአብሔር ብቻ ፈጣሪ እንዲባል ያደርገዋል። «ዓይናችሁን ወደ ላይ አንሥታችሁ ተመልከቱ፤ እነዚህን የፈጠረ ማን ነው? ሠራዊታቸውን በቊጥር የሚያወጣ እርሱ ነው። ሁሉንም በየስማቸው ይጠራቸዋል። በኃይሉ ብዛትና በከሃሊነቱ ብርታት አንድስ እንኳ አይታጣውም።» ይላል የእግዚአብሔር ቃል። ኢሳ ፵፥፳፮።

በእግዚአብሔር ረቂቅ ሥልጣንና ከሃሊነት የተፈጠረ ፍጥረት ሁሉ ሥርዓት ተሠርቶለት፤ ወሰን ተበጅቶለት ይኖራል። ከተሠራለት ሥርዓት አይወጣም፤ ከተደነገገለት ወሰን አያልፍም። ለይኩን ባለው መለኮታዊ ቃሉ እንደተፈጠረ ሁሉ፣ በመለኮታዊ ትእዛዙ ፀንቶ ይኖራል። መዝ ፴፪፥፬-፱፣ ዮሐ ፩፥፫።


«እነሆ ተራሮችን የሠራ ነፋስንም የፈጠረ፣. . . ንጋትን ጨለማ የሚያደርግ፣ በምድርም ከፍታዎች ላይ የሚረግጥ፣ ስሙ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ነው።» አሞ ፬፥፲፫። «ሰማያትን የፈጠረ እግዚአብሔር፣ እርሱም ምድርን የሠራና ያደረገ፤ ያፀናትም፣ መኖሪያ ልትሆን እንጂ ለከንቱ እንድትሆን ያልፈጠራት አምላክ እንዲህ ይላል። . . . ይናገሩ፤ ይቅረቡም፤ በአንድነትም ይማከሩ፤ ከጥንቱ ይህን ያሳየ ከቀድሞስ የተናገረ ማን ነው? ያሳየሁም፣ የተናገርሁም እኔ እግዚአብሔር አይደለሁምን? ከእኔ በቀር ሌላ አምላክ የለም። እኔ ጻድቅ አምላክና መድኃኒትም ነኝ ከእኔም በቀር ማንም የለምና ወደ እኔ ዘወር በሉ ትድኑማላችሁ። ኢሳ ፵፭፥፲፰-፳፪።


በዓለም ታላቁ መጽሐፍ በመባል የሚታወቀው መጽሐፍ ቅዱስ ጽሑፉን የሚጀምርልን የሰማይና የምድር ፈጣሪ እግዚአብሔር መሆኑን በማረጋገጥ ነው። ዘፍ ፩፥፩፣ ዮሐ ፩፥፫፣ መዝ ፴፪፥፮። ሰማይና ምድር ሲባልም፣ በሰማይና በምድር ያለውን ሁሉ፣ የሚታየውንና የማይታየውን፣ በሰው ዘንድ የታወቀውንና ገና ያለተደረሰበትን ፍጥረት ሁሉ አጠቃልሎ የያዘ ነው። ለዚህም ሁሉ ፈጣሪውና አስገኚው እግዚአብሔር በመሆኑ ዓለም የእግዚአብሔር ፍጥረት በመባል ይታወቃል። ዮሐ ፩፥፫፣ ቆላ ፩፥፲፮።


ማንኛውም የሥራ ውጤት ያለ ሠራተኛ ሊገኝ እንደማይችል ሁሉ፣ ማንኛውም ፍጡር ያለፈጣሪ አልተገኘም። ምሳሌውን እንመልከት። በባሕር ላይ የሚንሳፈፉ ግዙፋን መርከቦች፣ ከባዱንና ቀላሉን ሸክም ችለው፣ ሕዋውን እየቀዘፉ በሰማይ የሚበሩ አውሮፕላኖች፣ ውስብስቡን የዓለም ምሥጢር በትንሽ አካሉ አከማችቶ የያዘ ኮምፒውተር፣ በአጠቃላይ ዕፁብ ድንቅ የሚባሉ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ሁሉ የሰው ልጅ አእምሮ ተጨንቆ ተጠብቦ ያስገኛቸው የጥበብ ውጤቶች እንጂ በራሳቸው የተገኙ አይደለም። ታዲያ ከላይ የተጠቀሱ የሰው ልጅ መገልገያዎች በራሳቸው መገኘት የሚችሉ ካልሆነ እነዚህን ያስገኘ ረቂቅ የሰው ልጅ አእምሮ እንዴት ያለ ፈጣሪ ሊገኝ ይችላል ተብሎ ሊታሰብ ይችላል!!! ፈጽሞ አይታሰብም። ከታሰበም አስተሳሰቡ የስንፍና ውጤት ይሆናል። ለዚሁም ነው፣ «ሰነፍ በልቡ እግዚአብሔር የለም ይላል።» ተብሎ የተጻፈው። መዝ ፲፫፥፩፣ ኢሳ ፵፭፥፲፩።



እግዚአብሔር ከሃሊ ነው


ከሃሊ ማለት ሁሉን የሚችል፣ በፍጡር ዘንድ ፈጽሞ የማይቻልን ሁሉ ማድረግ የሚችል፣ ለችሎታው ወሰንና ገደብ የሌለበት፣ ይህን ይችላል ያን ግን አይችልም የማይባል ፍጹም ከሃሊ ማለት ነው። እግዚአብሔር፣ ሁሉም ነገር ከሥልጣኑ በታች በመሆኑ ሁሉም ይቻለዋል።


ይህን አስመልክቶ በዕብራይስጡ ቃል «ኤልሻዳይ» ተብሎ ተሰይሟል፤ ሁሉን የሚችል ማለት ነው። እግዚአብሔር ለአብራም በተገለጠለት ጊዜ፣ ከሃሊነቱን በሚያረጋግጥ ቃል እንደተገለጠለት መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ በማለት ያስተምረናል። «አብራምም የዘጠና ዘጠኝ ዓመት ሰው በሆነ ጊዜ እግዚአብሔር ለአብራም ተገለጠለትና፦ እኔ ኤልሻዳይ ነኝ፤ በፊቴ ተመላለስ፤ ፍጹምም ሁን። ቃል ኪዳኔንም በእኔና በአንተ መካከል አደርጋለሁ፤ እጅግም አበዛሃለሁ አለው።» ዘፍ ፲፯፥፩።


ፍጹም ከሃሊነት የእግዚአብሔር መለኮታዊ ሥልጣን በመሆኑ እግዚአብሔር ፍጹም ከሃሊ ይባላል። «በውኑ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለን? የዛሬ ዓመት ወደ አንተ እመለሳለሁ ሣራም ልጅን ታገኛለች።» ዘፍ ፲፰፥፲፬። «. . . ይህ በሰው ዘንድ አይቻልም፤ በእግዚአብሔር ዘንድ ግን ሁሉ ይቻላል አላቸው። ማቴ ፲፱፥፳፭-፳፮። ሉቃ ፩፥፴፭-፴፰።



እግዚአብሔር በሁሉ ምሉእ ነው


ምሉእ ማለት፣ ፍጹም የሆነ፣ ጉድለት /ሕፀፅ/ የሌለበት፣ በጊዜና በቦታ የማይወሰን፣ መቼም መች የነበረ ያለና የሚኖር ማለት ሆኖ የዚህ ባሕርይ ባለቤትም እግዚአብሔር ብቻ ነው።


እግዚአብሔር ከሁሉ በላይ ልዕልና ያለው አምላክ በመሆኑ ልዕልናውን ለመግለጽ ሲባል በሰማይ ያለ፣ ሰማያዊ አምላክ፣ ሰማያዊ አባት እየተባለ ይጠራል። ማቴ ፮፥፱-፲፣ ፲፰፥፲።


እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ይወስናል እንጂ ሰማይና ምድር እግዚአብሔርን አይወስኑም። ከፍታዎችና ጥልቆች ሁሉ በእግዚአብሔር መዳፍ ናቸው፤



ማስረጃ

«ከመንፈስህ ወዴት እሄዳለሁ፤ ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ፤ ወደ ሰማይ ብወጣ፣ አንተ በዚያ ነህ፤ ወደ ሲኦልም ብወርድ በዚያ አለህ። እንደ ንሥር የንጋትን ክንፍ ብወስድ እስከ ባሕርም መጨረሻ ብበር በዚያ እጅህ ትመራኛለች፤ ቀኝህም ትይዘኛለች። በውኑ ጨለማ ትሸፍነኛለች ብል፣ ሌሊት በዙሪያዬ ብርሃን ትሆናለች።» መዝ ፻፴፰፥፯-፲፪።

«እኔ የቅርብ አምላክ ነኝ እንጂ የሩቅ አምላክ አይደለሁም። ሰው በስውር ቢሸሸግ፤ እኔ አላየውምን? ሰማይንና ምድርንስ የሞላሁ እኔ አይደለሁምን? ይላል እግዚአብሔር።» ኤር ፳፫፥፳፫።

«የእግዚአብሔርን ጥልቅ ነገር /ምሥጢር/ ልትመረምር ትችላለህን? ወይስ ሁሉን የሚችል አምላክን ፈጽመህ ልትመረምር ትችላለህን? ከሰማይ ይልቅ ከፍ ይላል፤ ምን ልታደርግ ትችላለህ? ከሲኦልም ይልቅ ይጠልቃል፤ ምን ልታውቅ ትችላለህ? ርዝመቱ ከምድር ይልቅ ይረዝማል፤ ከባሕርም ይልቅ ይሰፋል።» ኢዮ ፲፩፥፯-፱።

«ውኆችን በእፍኙ የሰፈረ፣ ሰማይንም በስንዝር የለካ የምድርንም አፈር በመስፈሪያ ሰብስቦ የያዘ፣ ተራሮችን በሚዛን፣ ኮረብቶችንም በሚዛኖች የመዘነ ማነው?  . . . እነሆ አሕዛብ በገንቦ እንዳለች ጠብታ ናቸው። . . . አሕዛብ ሁሉ በፊቱ እንዳልነበሩ ናቸው። ከምናምን እንደሚያንሱ እንደ ከንቱ ነገርም ይቈጥራቸዋል። እንግዲህ እግዚአብሔርን በማን ትመስሉታላችሁ? ወይስ በምን ምሳሌ ታስተያዩታላችሁ? . . .።» ኢሳ ፵፥፲፪-፲፰።
 

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 


Written By: admin
Date Posted: 1/10/2012
Number of Views: 7004

Return

  
Copyright 2016 by Mahibere Kidusan USA Center  | Terms Of Use | Privacy Statement