View in English alphabet 
 | Friday, March 29, 2024 ..:: መቅድም ::.. Register  Login
  

ጰራቅሊጦስ

በትራክት መልክ የተዘጋጀውን መልእክት ለማግኘት እዚህ ይጫኑ

በዲ/ን ዶ/ር ንዋይ ገሠሠ

በዓለ ጰራቅሊጦስ ወይም በዓለ ጰንጠቆስጤ ከዘጠኙ የጌታችን ዐበይት በአላት አንዱ ሲሆን መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት የወረደበትን ቀን የምናስብበት በዓል ነው። ጰራቅሊጦስ የግሪክ ቃል የሆነ የመንፈስ ቅዱስ መጠሪያ ነው። ትርጉሙም በጐን የሚቆም፣ የሚረዳ፣ የሚያጽናና ማለት ነው። አበው መንጽሂ /የሚያነጻ፣ የሚቀድስ/ መጽንሂ /የሚያጸና፣ የሚያበረታ/ በማለት ይገልጹታል። ጰንጠቆስጤ የሚለውም የግሪክ ቃል ሲሆን “ፔንዲኮንዳ” ሃምሳ “ፔንዲኮስቲ” ሃምሳኛ ማለት ነው። በዓሉ ጌታችን ባረገ በአሥረኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ በተነሳ በሃምሳኛው ቀን ይከበራል።

የበዓሉ የትመጣ
እስራኤል ከግብጽ ከወጡና ሕገ ኦሪት ከተሰጠቻቸው ጊዜ ጀምረው በዓለ ፋሲካን ለማክበር በኢየሩሳሌም ይሰበሰባሉ። ፋሲካ ለእስራኤል የነፃነት በዓላቸው ስለሆነ በስደት ምክንያት ወደ ተለያዩ ሀገሮች ከተበተኑ በኋላም እንኳን ካሉበት በመምጣት በዓሉን የሚያከብሩ ሲሆን ከፋሲካ ማግስት ጀምረው ሃምሳውን ቀን በዓል አድርገው አገር የቀረበው በየአገሩ እየሄደ አገር የራቀበት ስንቁን ይዞ ከዚያው ከኢየሩሳሌም ይሰነብታል። በሃምሳኛው ቀን በዘፀ ፴፬፥፳፪፣ በዘሌዋ ፳፫፥፲-፲፯ በታዘዙት መሠረት በዓለ ሰዊትን /የእሸት በዓልን/ ካመረቱት ምርት በኩራቱን ለመሥዋዕት በማቅረብ ያከብራሉ። በዓለ ፋሲካን ለማክበር ከዝርወት ተሰብስበው የነበሩ አይሁድ ሁሉ ወደየመጡበት የሚመለሱት ይህን በዓለ ሰዊትን ካከበሩ በኋላ ነው። በዓለ ሰዊትን በዝርወት የተሰበሰቡና በዚያውም የሚኖሩ አይሁድ አብዛኛውን ጊዜ በዓል የሚያከብሩት በደብረ ጽዮን ነው።

በዚሁ ልማድና ሥርዓት መሠረት ጌታችን በመሥቀል ተሰቅሎ ድኅነተ ዓለምን በፈጸመበት ዓመት እስራኤላዊያን በዚች በደብረ ጽዮን በዓለ ሰዊትን ለማክበር ተሰብስበው እንዳሉ ሐዋርያት ደግሞ ጌታችን የነገራቸውን ተስፋ እየተጠባበቁ በዚሁ በደብረ ጽዮን በቅዱስ ማርቆስ እናት ቤት ውስጥ ተሰብስበው ነበር። ይህች ቀን ጌታ ባረገ አሥረኛው ቀን ነበረች። በዚህች ዕለት ጠዋት አይሁድ የቀድሞውን በዓል ሲያከብሩ ለሐዋርያት ጌታ የነገራቸው የተስፋ ቃል ተፈጸመላቸው፤ መንፈስ ቅዱስ ተሰጣቸው /ሐዋ ፪፥፩-፬/ በማለት በሐዋርያት ሥራ ላይ ጽፎልናል። ስለዚህም ቅዱሳን ሐዋርያት በዲድስቅሊያ 31 “ከዕርገቱ ቀን በኋላ ታላቅ በዓል ይደረግ፤ በዚህች ቀን በሦስተኛው ሰዓት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጰራቅሊጦስን ልኮልናልና እኛም በእርሱ ስጦታዎች ተሞላን አዳዲስ ቋንቋን ተናገርን” በማለት በዓሉን በቤተ ክርስቲያን እንድናከብር ሥርዓትን ሠርተዋል። በዚህም መሠረት በነቢያትና በሐዋርያት ትምህርት ላይ የታነጸችው ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንኑ በዓል ዛሬም ድረስ ታከብራለች።

ትንቢት
በቅዱስ መጽሐፍ ስለ መንፈስ ቅዱስ የተገለጠውን ስናይ የአብና የወልድ ሕይወታቸው የሆነ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለዓለሙ ሁሉ ሕይወትን የሚያድል ስለሆነ ምሉዕ ሆኖ በሁሉ ቦታ እንዳለ “የእግዚአብሔርም መንፈስ በውሃ ላይ ሰፍፎ ነበር´’ /ዘፍ ፩፥፪/ በማለት ይገልጻል። ይህ የእግዚአብሔር መንፈስ በዘመናት ሁሉ ከእግዚአብሔር ወዳጆች ጋር በመሆን ምግባር ትሩፋት እንዲሠሩ ያደርጋል። ሆኖም ግን የሰው ልጆች ኃጢአትን በሰሩ ጊዜ በዓለም ላይ ምሉዕ የነበረው የእግዚአብሔር መንፈስ ከሰው እንደራቀ ቅዱስ መጽሐፍ እንዲህ በማለት ይገልጽልናል። እግዚአብሔርም መንፈሴ በሰው ላይ ለዘላለም አይኖርም፥ እርሱ ሥጋ ነውና፤ ዘመኖቹም መቶ ሃያ ዓመት ይሆናሉ አለ /ዘፍ ፮፥፫/። ኋላም ሰውን ወዳጅ የሆነው ልዑል አምላካችን የሰውን ልጅ በሞቱ ሊያድነውና በቅዱስ መንፈሱም ሊያጸናውና ሊያጽናናው መፍቀዱን በነቢያት አድሮ ትንቢት አናግሯል። ነቢዩ ኢሳይያስ በትንቢቱ “ከእሴይ ግንድ በትር ይወጣል። ከሥሩም ቁጥቋጥ ያፈራል። የእግዚአብሔር መንፈስ የጥበብና የማስተዋል መንፈስ የምክርና የኃይል መንፈስ የዕውቀትና እግዚአብሔርን የመፍራት መንፈስ ያርፍበታል።” /ኢሳ ፲፩፥፪/ በማለት ተናግሯል። በተለይም የመንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት መውረድ “መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ አፈስሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢትን ይናገራሉ፥ ሽማግሌዎችሁም ሕልምን ያልማሉ ጎበዞቻችሁም ራእይ ያያሉ…” /ኢዩ ፪፥፳፰/ የሚል የነቢይ ቃል ነበረ።

የትንቢቱ ፍጻሜ
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ስብከቱ የመረጣቸው ደቀ መዛሙርት በመጀመሪያ አካባቢ ይከተሉት የነበረው ምድራዊ ሹመትና ሥልጣን ከመፈለግ አንጻር ነበረ። ይሁን እንጂ እየዋሉ እያደሩ ቃሉን ሲሰሙ ለምድራዊ ክብር ሳይሆን ለሰማያዊ ክብር መጠራታቸውን ነግሯቸዋል። ይሁን እንጂ ጌታችን ወደዚህ ዓለም የመጣበትን የሰውን ልጅ ከዘላለማዊ ሞት የማዳን ዋነኛ ዓላማ ለመፈጸም ተቃርቦ ጥቂት ቀናት ሲቀሩት ደቀ መዛሙርቱ የፍርሃትና የመታወክ ልብ ነበራቸው። ይህ የሚታወክ ልቦና ሊረጋጋ የሚችለው በሚኖራቸው ፍጹም እምነት እንደሆነ ለማስረገጥ “ልባችሁ አይታወክ በእግዚአብሔር እመኑ በእኔ ደግሞ እመኑ” /ሐዋ ፲፬፥፩/ ብሏቸዋል። ፍጹም የሆነ እምነት ያለው ሰው አይረበሽም አይታወክም። የሚያስፈራው የሚያስደነግጠው ነገር አይኖረውም።
 
ጌታ ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት ደቀ መዛሙርቱን  “ኃይልን እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ቆዩ” /ሉቃ ፳፬፥፵፱/ ባላቸው መሠረት የተገባላቸውን ቃል ኪዳን በተስፋ ሲጠብቁ ቆይተዋል። ይህ ኃይል መንፈሳዊና ሰማያዊ ኃይል ነው ይህም የሚገኘው ከእግዚአብሔር ብቻ ነው። ይህንን ኃይል ለማግኘት እግዚአብሔርን በትዕግስት ሆኖ ደጅ መጥናት ያስፈልግ ነበረ። ስለዚህም ደቀ መዛሙርቱ “ሁሉም በአንድ ልብ ሆነው ሳሉ ድንገት እንደሚነጥቅ ዐውሎ ነፋስ ከሰማይ ድምጽ መጣ፣ ተቀምጠው የነበረበትን ቤት ሞላው እንደ እሳትም የተከፋፈሉ ልሳኖች ታዩአቸው በእያንዳንዳቸው ላይ ተቀመጡባቸው  በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው መንፈስም ይናገሩ ዘንድ እንደ ሰጣቸው በሌላ ልሳኖች ይናገሩ ጀመር” እንዲል /ሐዋ ፪፥፪-፬/። ሁሉም በአንድ ልብ ነበሩ፤ የተከፋፈለ ሃሳብ አልነበራቸውም። ዛሬ የብዙዎቻችን ልብ ቀርቶ የእያንዳንዳችን ልብ እንኳን አንድ አይደለም። በብዙ ነገር ልቦናችን ይከፋፈላል። እግዚአብሔር ኅብረትና ፍቅር ከሌላቸው ሰዎች ጋር ምንም አይሠራም።
 
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ “አብ በስሜ የሚልክው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው ኣጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል። እኔም የነገርኳችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል።” /ዮሐ ፲፬፥፳፮/ ባለው መሠረት ደቀ መዛሙርቱን የሚያጽናና፣ የሚያረጋጋና ምሥጢርን የሚገልጽ ጰራቅሊጦስ መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል። ደቀ መዛሙርቱ ይህንን የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ በበዓለ ሃምሳ ካገኙበት ጊዜ ጀምሮ የተሰጣቸውን የምሥራች የሆነውን ወንጌል ለፍጥረት ሁሉ ለመስበክና ኃላፊነታቸውን በሚገባ ለመወጣት ራሳቸውን ለእግዚኣብሔር የተቀደሰ አድርገው አቅርበዋል። በዚሁ ዕለት መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት ከወረደላቸውና የመንፈስ ቅዱስ ማደርያ ከሆኑ በኋላ በመንፈስ ብርቱ ሆነዋል፣ በዕውቀት ጎልምሰዋል፣ ከብልየት ታድሰዋል።
 
በዕለቱ ከተለያዩ የዓለም አገራት በዓለ ሃምሳ የተባለውን ታላቅ በዓል ለማክበር ኢየሩሳሌም የተሰበሰቡ ብዛት ያለው ሕዝብ ሐዋርያት በቋንቋቸው ወንጌልን ሲሰብኩ በመስማታቸው ተደንቀዋል። “እያንዳንዱም በገዛ ቋንቋቸው ሲናገሩ ይሰማ ስለነበር የሚሉትን አጡ ተገርመው ተደንቀውም እንዲህ አሉ፥ እነሆ እነዚህ ሁሉ የሚናገሩ የገሊላ ሰዎች አይደሉምን እኛም እያንዳንዳችን  የተወለድንበትን የገዛ ቋንቋችንን እንዴት እንሰማለን” /ሐዋ ፪፥፯-፰/ በማለት በመገረም ይናገሩ ነበር። በዚህ ዕለት ቅዱስ ጴጥሮስ በሕዝቡ መሐል ተገኝቶ አይሁድ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዴት አድርገው መከራ እንዳጸኑበት፣ በመስቀል ላይ እንደሰቀሉት፣ እንደገደሉት እርሱ ግን ሞትን ድል አድርጎ ተነሳ እኛ ደግሞ ለዚህ ምስክሮች ነን ብሎ ማንንም ሳያፍርና ሳይፈራ ያስተምር ነበር። ባስተማረው ትምህርት ልባቸው የተነካ ብዛት ያላቸው ሰዎች ሐዋርያትን ወንድሞች ሆይ ምን እናድርግ ሲሉ ጠይቀዋል። ቅዱስ ጴጥሮስ “ንስሐ ግቡ ኃጢያታችሁም ይሰረይ ዘንድ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ” በማለት ንስሐ እንዲገቡና የተስፋው ቃል ተሳታፊዎች እንዲሆኑ አስተምሯቸዋል።

ቃሉን ሰምተው ንስሐ የገቡና የተጠመቁ ሰዎች ቁጥራቸው ሦስት ሺህ ያህሉ ነበር። ቃሉንም የተቀበሉ ተጠመቁ፥ በዚያን ቀን ሦስት ሺህ የሚያህል ነፍስ ተጨመሩ፤ በሐዋርያትም ትምህርትና በኅብረት እንጀራውንም በመቁረስ በየጸሎቱም ይተጉ ነበር። /ሐዋ ፪፥፵፩-፵፪/። ያመኑት ሁሉ አብረው በኅብረት ይኖሩ ነበር ያላቸውን ሀብት ንብረት ሳይቀር አንድ ላይ አደረጉ። በመካከላቸው መለያየት አልነበረም። ሀብታም ደሃ ትንሽ ትልቅ የሚል ልዩነት አልነበረም። ሁሉም እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ እንደ አንድ ልብ መካሪ ነበሩ። ሁለት ሦስት ሆናችሁ በስሜ በምትሰበሰቡበት በመካከላችሁ እገኛለሁ ብሎ ነበረና በስሙ አንድ ሆነው በፍቅር በመገኘታቸው “ስጦታን ለሰው ልጅ ሰጠህ” /መዝ ፷፯፥፲፰/ የሚለው የዳዊት ቃል በእነርሱ ላይ ተፈጽሟል። ሰማያዊ በረከትንና ጸጋውን ሊቀበሉ ችለዋል። በዚህም ስጦታ የመንፈስ ልዕለናን ይዘው ጨለማውን ዓለም በወንጌል አብርተዋል። ኃይለ አጋንንትን ድል አድርገዋል። አላውያን ነገሥታትን አሳፍረዋል።

ቤተ ክርስቲያን በዚህ ቀን በመንፈስ ቅዱስ ተሞልታለች። ልጆች የሆንን ሁላችንም በአርባና በሰማንያ ቀን ስንጠመቅ ነው ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማሕፀነ ዮርዳኖስ የተወለድነውና ከሥላሴ ልጅነት ያገኝነው። ይህን በጥምቀት ጊዜ ያገኘነውን ጸጋ አክብረን ልንይዘው ይገባናል። “በትሕትና ሁሉና በየዋህነት በትዕግስትም እርስ በርሳችሁ በፍቅር ታገሱ በሰላም ማሰማሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ” /ኤፌ ፬፥፪-፫/ እንዲል እንደተሰጠን የጸጋ ስጦታ መጠን ቤተ ክርስቲያንን በፍቅር በአንድነት ሆነን ልናገለግል ይገባናል። እርሱ በማይታበለው ቃሉ ወላጆች እንደሌላቸው ልጆች አልተዋችሁም ያለ ጌታ ዛሬም በደሙ የዋጃትን የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆችን አይተዋቸውም። ብቻ እኛ በቤቱ ጸንተን በፍቅር እንኑር። ሁሌም እርሱ ከእኛ ጋር ይኖራል። ለዚህም የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ጸጋ የእመቤታችን ኣማላጅነት የሐዋርያት ረድኤት በረከት አይለየን። አሜን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Written By: admin
Date Posted: 6/3/2012
Number of Views: 5028

Return

  
Copyright 2016 by Mahibere Kidusan USA Center  | Terms Of Use | Privacy Statement