View in English alphabet 
 | Thursday, March 28, 2024 ..:: መቅድም ::.. Register  Login
  

ትምህርተ ሃይማኖት ኦርቶዶክሳዊት

ወልድ ዋሕድ /ክፍል ፫/


በሊቀ ካህናት ኃይለሥላሴ ዓለማየሁ ደስታ


እግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ነው

ዘለዓለማዊ የሚለው ቃል ከቋንቋነቱ አኳያ ሲታይ የእግዚአብሔርን ባሕርይ ለመግለጽ ደካማ ወይም አናሳ ቃል ሆኖ የሚታይ ይመስላል። በእርግጥም የቃሉ ገላጭነት የደከመ ወይም የጠበበ ነው። ይሁንና ሌሎች ቃላት ቢሆኑም የእግዚአብሔርን መለኮታዊ ባሕርይ በፍጹምነት የመግለጽ ብቃት አላቸው ብሎ መገመት አስቸጋሪ መሆኑ አይቀርም።

የሆነ ሆኖ ግን ዘለዓለማዊ ከሚለው ቃል መረዳት የሚቻለው፣ እግዚአብሔር አምላክ ቅድመ ዓለም የነበረ፣ በማዕከለ ዓለም ያለ፣ ዓለምን አሳልፎ የሚኖር፣ ፍጻሜ /መጨረሻ/ መነሻና መድረሻ የሌለው፣ እርሱ ራሱ መጀመሪያና መጨረሻ፣ የሆነ፣ የነበረ፣ ያለና የሚኖር ኅልፈትና ሽረት የሌለበት አምላክ መሆኑን ነው።


ማስረጃ


«ተራሮች ሳይወለዱ፥ ምድርም፥ ዓለምም ሳይሠሩ፥ ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም ድረስ አንተ ነህ።» መዝ ፹፱፥፪።

«የእስራኤል ንጉሥ እግዚአብሔር፣ የሚቤዥም የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እኔ ፊተኛ ነኝ እኔም ኋለኛ ነኝ፥ ከእኔ ሌላም አምላክ የለም።» ኢሳ ፵፬፥፮።

«ሙሴም አግዚአብሔርን፦ እነሆ እኔ ወደ እስራኤል ልጆች በመጣሁ ጊዜ የአባቶቻችሁ አምላክ ወደ እናነተ ላከኝ ባልሁም ጊዜ ስሙስ ማነው ባሉኝ ጊዜ ምን እላቸዋለሁ? አለው። እግዚአብሔርም ሙሴን ያለና የሚኖር እኔ ነኝ አለው።» ዘጸ ፫፥፲፫።
 
«ያለውና የነበረው የሚመጣውም ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ አልፋና ዖሜጋ እኔ ነኝ ይላል።» ዮሐ ራእ ፩፥፰።


እግዚአብሔር ቅዱስ ነው

ቅዱስ ማለት ልዩ፣ ንጹሕ፣ ጽሩይ፣ ከክፉ ነገር ከረከሰ ነገር ሁሉ የተለየ ማለት ነው። እንደዚህ ያለ ቅድስና የባሕርይ ገንዘቡ የሆነ እግዚአብሔር ብቻ ነው። ሌላው ፍጥረት ቅዱስ ቢባል ቅድስና ከእግዚአብሔር ስለሚሰጠው ነው። እግዚአብሔር ግን ከሌላ የሚያገኘው፣ የሚጨመርለት ወይም የሚቀነስበት አንድም ነገር ፈጽሞ የለም።

ፍጡርንና ፈጣሪን በአንድ ዓይነት አገላለጽ «ቅዱስ» እያልን ስንጠራ የቋንቋ እጥረት ሊሆን ይችላል እንጂ ባሕርየ ፈጣሪ ከባሕርየ ፍጡር ፈጽሞ የተለየ በመሆኑ የእግዚአብሔር ቅድስናም ከፍጡር ቅድስና ልዩ ነው። የተሻለ ስፋት ያላቸው አንዳንድ ቋንቋዎችም በፍጡርና በፈጣሪ መካከል ያለውን የቅድስና ልዩነት ለይተው ይጠቀማሉ።

ባጭር አገላለፅ ባሕርየ ፍጡር /የፍጡር ባሕርይ/፦
•    ጽድቅና ኃጢአት
•    እውነትና ሐሰት
•    ትሕትናና ትዕቢት
•    ክፋትና ደግነት
•    ሕይወትና ሞት
•    ሹመትና ሽረት
•    ፍትሐዊነትና ፍትሕ አልቦነት
•    ርኅራኄና ጭካኔ
•    ፍቅርና ጥላቻ
•    ቁጣና ትዕግሥት ወዘተ… እየተፈራረቁበት ሲወድቅ ሲነሳ የሚኖር ሕይወት ነው። ፍጡር በአብዛኛው ጊዜ በእግዚአብሔር ቸርነትና መግቦት የሚኖር በመሆኑ ቅድስናው የእግዚአብሔር ምሕረት ታክሎበት የሚገኝ ካልሆነ አስቸጋሪ ይሆናል።

«ንጹሕ ይሆን ዘንድ ሰው ምንድን ነው? ጻድቅስ ይሆን ዘንድ ከሴት የተወለደ ምንድን ነው? እነሆ በቅዱሳኑ ስንኳ አይታመንም ሰማያትም በፊቱ ንጹሐን አይደሉም። ይልቁንስ አስጸያፊና የረከሰ፥ ኃጢአትንም እንደ ውኃ የሚጠጣ ሰው ምንኛ ያንስ?» ኢዮ ፲፭፥፲፬-፲፮።


ማስረጃ

«ንጉሡ ዖዝያን በሞተበት ዓመት እግዚአብሔርን በረጅምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ተቀምጦ አየሁት፥ የልብሱም ዘርፍ መቅደሱን ሞልቶት ነበር። ሱራፌልም ከእርሱ በላይ ቆመው ነበር፥ ለእያንዳንዱም ስድስት ክንፍ ነበረው በሁለት ክንፍ ፊቱን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ እግሮቹን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ ይበር ነበር። አንዱም ለአንዱ፦ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች እያለ ይጮህ ነበር።» ኢሳ ፮፥፩-፫።

«እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ ለእስራኤል ልጆች ማኅበር ሁሉ እንዲህ በላቸው፦ እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተ እቅዱሳን ሁኑ።» ዘሌ ፲፱፥፩-፪።

«ዳሩ ግን፦ እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ።» ፩ኛ ጴጥ ፩፥፲፮።


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም በቅዱሳን አባቶች በቅዱስ ያሬድና በአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ አማካይነት ከእግዚአብሔር ባገኘችው ጸጋና በረከት በማሕሌትዋ፣ በሰአታትዋና በቅዳሴዋ እንደ መላእክት ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር… እያለች ዘወትር ፈጣሪዋን ታመሰግናለች።


ማስረጃ

•    «ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት።»
•    «ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ጸባዖት ፍጹም ምሉእ ሰማያተ ወምድረ ቅድሳተ ስብሐቲከ።»
•    «ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ዘእምቅድመ ዓለም ሀሎ ወይሄሉ እስከ ለዓለም።»
•    «ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ዘይሴባሕ እምትጉሃን ወይትቄደስ እምቅዱሳን።»
•    «ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር የአማልክት አምላክ ዘወትር /ሁልጊዜ/ በሰማይና በምድር ያለ፤ የሚኖር።»

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እንዲህ ዓይነቱ የማያቋርጥ ምስጋናዋ ከቅዱሳን መላእክት ተርታ ሊያሰልፋት ችሏል።


እግዚአብሔር ፍጹም ነው

ፍጹምነት የእግዚአብሔር ልዩ የባሕርይ ገንዘብ ነው። ፍጹም ማለትም በሁሉ ዘንድ በሁሉ አቅጣጫ የሚገኝ ሕፀፅ /ጉድለት/ የሌለበት፣ ነውር የማይገኝበት፣ በሁሉም የመላ፣ የተካከለ፤ መሳይ፣ ተመሳሳይ፣ አምሳያ የማይገኝለት፤ ኃያል፣ አሸናፊ፣ መጋቢ ሠራዒ፣ ሁሉን የሚገዛ፣ ወዘተ….. ማለት ነው።

የባሕርይ ፍጹምነት የእግዚአብሔር የግል ገንዘቡ በመሆኑ እንደ እግዚአብሔር ያለ በፍጹምነት የሚገኝ ማንም የለም።

«እግዚአብሔር በመንገዱ ሁሉ ምስጉን ነው። የአማልክት አምላክ ፍጹም አሸናፊ ነው። የሌለበት ጊዜ የለም፤ የታጣበትም ጊዜ የለም። በመለኮቱ ግን ፈጽሞ የታየበት ጊዜ የለም። እርሱን ማየት የሚችል የለም። አነዋወሩም እንደምን እንደሆነ የሚያውቅ /ማወቅ የሚችል/ የለም።» እንዳሉ ፫፻፲፰ አበው ርቱዓነ ሃይማኖት /ቅዳሴ ዘሠለስቱ ምእት/።

«አነሆ እግዚአብሔር ታላቅ ነው፥ እኛም አናውቀውም [መርምረን አንደርስበትም]። የዘመኑም ቁጥር አይመረመርም።» ኢዮ ፴፮፥፳፮።


ማእምር

ማእምር ማለት ሁሉን የሚያውቅ፣ ሁሉን የሚረዳ፣ ድርሱን፣ ርግጡን፣ ልኩን የሚያውቅ ወይም ያወቀ ማለት ነው።
 
ዕውቀት ከባሕርይና ከትምህርት ይገኛል። የትምህርት ዕውቀት ማለትም ያልለመዱትን ነገር መልመድ፣ መረዳት፣ መገንዘብ ማለት ነው። ከትምህርት የሚገኝ ዕውቀት ከትንሽ ወደ ትልቅ፣ ግልጽ ከሆነ መነሻና መድረሻ ወደማይገኝለት ወይም ፍጻሜ ወደ ሌለው ውስብስብ ነገር አያደገ፣ እየመጠቀና እየረቀቀ የሚሔድ ልምድ ነው። ሌላው ማወቅ የሚባለው ደግሞ አንድን ነገር ከመሆኑ በፊት፣ በሆነ ጊዜና ከሆነም በኋላ ያለውን ነገር ያመለክታል።

እንዲህ ያለው ዕውቀት ፍጡር ከፈጣሪ በተሰጠው አእምሮ መሠረት የሚያገኘው ክሂሎት /ችሎታ/ ይባላል። ሀብተ ትንቢት የተሰጣቸው የእግዚአብሔር ሰዎችም መጻእያትንና ሐላፊያትን አውቀው ትንቢት ይናገራሉ፣ ያስተምራሉ።

ከባሕርይ የሚገኝ ዕውቀት ደግሞ አስተማሪ፣ መካሪ፣ አዘካሪ ወይም አስታዋሽ ሳያስፈልግ በተፈጥሮ ማለትም በአእምሮ ጠባይዕ የሚገኝ ከእግዚአብሔር የተሰጠ ጸጋ ነው። በአጠቃላይ ፍጡር የሆነውን ነገር አይቶ ሰምቶ፣ ተምሮ ተመራምሮ ያውቃል፤ ሐላፊያትን መጻእያትንም እንደ ቅዱሳን ነቢያት መንፈስ እግዚአብሔር ገልጾለት /አናግሮት/ ያውቃል ይናገራል ይመሰክራል። ኢሳ. ፯፥፲፬፣ ፱፥፮። የፍጡር ዕውቀት ሁሉም በዓረፍተ ዘመን የተገደበ ነው፤ ገደብ የሌለው የፍጡር ዕውቀት ፈጽሞ የለም። መገኛውም እግዚአብሔር ነው።

የእግዚአብሔር ዕውቀት ከዚህ ሁሉ ፈጽሞ የተለየ ነው። ነገሮች ሁሉ ከመታሰባቸው፣ ፍጥረታት ሁሉ ከመፈጠራቸው፣ መጻእያት ሁሉ ከመድረሳቸው /ከመሆናቸው/፣ ሓላፊያት ሁሉ ካለፉ ከጠፉ በኋላ በሕሊና አምላክ አሉ፤ በእግዚአብሔር ዘንድ ይታወቃሉ። የእግዚአብሔርን ዕውቀት ሊገድብ የሚችል ምንም ዓይነት ምክንያት የለም።


ማስረጃ

«ውእቱሰ የአምር ሕሊና ሰብእ እምቅድመ ኵነታ።»

«ልብንና ጥልቅንም መርምሮ ያውቃቸዋል ምክራቸውንም ሁሉ ያውቃል እግዚአብሔር የልቡና አሳብን ሁሉ ያውቃል… ያለፈውንም የሚመጣውን እሱ ይናገራል የተሠወረውንም ምሥጢር ይገልጣል። ከእግዚአብሔር ምክር ሁሉ የሚያመልጥ የለም ከነገሩ ሁሉ አንዲት ቃል ስንኳ የሚሰወረው የለም።» ሲራ ፵፪፥፲፰-፳።

«አቤቱ መረመርኸኝ፥ አውቅኸኝም። አንተ መቀመጤንና መነሳቴን አወቅህ አሳቤን ሁሉ ከሩቅ አስተዋልህ። ፍለጋዬንና ዕረፍቴን አንተ መረመርህ መንገዶቼን ሁሉ ቀድመህ አወቅህ፥… አቤቱ፥ አንተ እነሆ የቀድሞውንና የኋላውን አወቅህ… እውቀትህ ከእኔ ይልቅ ተደነቀች በረታች፥ ወደ እርስዋም ለመድረስ አልችልም።» መዝ ፻፴፰፥፩-፮።

«ነገር ግን ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ ያውቅ ነበር ስለ ሰውም ማንም ሊመሰክር አያስፈልገውም ነበርና አይተማመናቸውም ነበር ራሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና።» ዮሐ ፪፥፳፭፣፮፥፷፬፤ ማቴ ፱፥፬።

Written By: admin
Date Posted: 9/29/2012
Number of Views: 7526

Return

  
Copyright 2016 by Mahibere Kidusan USA Center  | Terms Of Use | Privacy Statement