View in English alphabet 
 | Friday, April 26, 2024 ..:: መቅድም ::.. Register  Login
  

በፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽዖ” በሚል ርዕስ ልዩ  ዓውደ ጥናት ተካሄደ።

“የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽዖ” በሚል ርዕስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል ከፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ እና የሴሜቲክና የአፍሮ እስያ ከፍተኛ ምርምርና ጥናት ተቋም (The Institute for Advanced Semitic Studies and Afroasiatic Studies) ክፍል ጋር በመተባበር ሐምሌ/24 2008 ዓም በፕርንስተን ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ዓውደ ጥናት አካሄደ። ዓውደ ጥናቱ በዋናነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በተለያየ ዘርፍ ለኢትዮጵያና ለዓለም ያበረከተችውን አስተዋጽዖ በጥልቀት የዳሰሰ ነው። 

በዓውደ ጥናቱ ላይ በአቅራቢነት ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሃቅ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መምህራን እና የውጭ ዜጎች የተሳተፉ ሲሆን የቤተ ክርስቲያን አስተዋጽዖ በሀገሪቷ ሰላምና ልማት እንዲጠናከር ከማድረግ አንጻር ፤ የተለያዩ የእምነት ተቋማትና ኅብረተሰብ በማኅበራዊ ሕይወት ውስጥ ተቻችለውና ተከባብረው ለዘመናት እንዲኖሩ ከማስቻል አንጻር ፤ እንዲሁም በሥነ ጽሑፍ ፣ በቋንቋ ፣ በሥነ ዜማ እና በተለያዩ መስኮች ላይ ትኩረት ያደረጉ ዝግጅቶች ቀርበው ውይይቶች ተካሂደዋል።

በዚህ ዓውደ ጥናት ላይ ከፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲና ከተለያዩ ተቋማትና አካባቢዎች የመጡ ተሳታፊዎች የተገኙበት ሲሆን መርሐ ግብሩ በአማርኛ እና በእንግሊዘኛ ቋንቋዎች ተካሂዷል። ዓውደ ጥናቱን በተመለከተ አንዳንድ ተሳታፊዎች  በሰጡት አስተያየት ይህ ዓይነቱ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለተቀረው ዓለም የማስተዋወቁ ሥራ ማኅበሩ አጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበው አስፈላጊነቱ ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን በውጪ ሀገር ለሚኖረው ኢትዮጵያዊ ሁሉ ኩራትና ለሀገራችንም በብዙ መልኩ እንደሚጠቅም ገልጸዋል። በመጨረሻም ለዚህ መርሐ ግብር መሳካት ቦታ በማመቻቸት ፣ በቁሳ ቁስ አቅርቦት እና  አስተርጓሚ በማዘጋጀት የፕሪንስተን ዩኒቨርሲቲ ላደረገው ከፍተኛ ትብብር እንዲሁም ለጥናት አቅቢዎችና ተሳታፊዎች የማኅበሩ ተወካይ ምስጋናቸውን አቅርበው ወደፊትም ይህን መሰል ዓውደ ጥናቶችን ማዕከሉ በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ካላቸው ዩኒቨርሲቲዎችና ተቋማት ጋር በተጠናከረ ሁኔታ እንደሚያካሂድ ገልጸዋል።


Written By: useducation
Date Posted: 8/4/2016
Number of Views: 1998

Return

  
Copyright 2016 by Mahibere Kidusan USA Center  | Terms Of Use | Privacy Statement