View in English alphabet 
 | Thursday, May 2, 2024 ..:: መቅድም ::.. Register  Login
  

ቅዱሳን መላእክት - ስግደት ለመላእክት

መስገድ የሚለው ቃል መዋረድ፣ ማጐንበስ፣ መንበርከክ፣ መደፋት፣ በግንባር መውደቅ፣ ግንባርን ምድር አስነክቶ መሬት ስሞ መመለስ ነው በማለት የአለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት ያትታል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ስግደት የአምልኮና የጸጋ ተብሎ ይከፈላል፡፡ የአምልኮ ስግደት ለእግዚአብሔር ብቻ የሚቀርብ ሲሆን የጸጋ ስግደት ደግሞ እግዚአብሔር ላከበራቸው ቅዱሳን ሰዎችና መላእክት የሚቀርብ ነው፡፡

ለቅዱሳት መላእክት የምናቀርበው ስግደት ከላይ እንደተገለጸው የጸጋ ስግደት ነው፡፡ ጸጋ የሚለው ቃል በቁሙ ሲተረጎም ሀብት፣ መልካም ሥጦታ፣ ዕድል ፈንታ፣ ትምህርት፣ ብዕል፣ ክብር፣ ሞገስ የቸርነት ሥራ አለዋጋ የሚሰጥና የሚደረግ ማለት ነው፡፡[1] የጸጋ ስግደት ስንል እግዚአብሔር የሰጣቸውን ክብርና ሞገስ አምኖ መንበርከክ ነው፡፡ ይህም ራስን ለእግዚአብሔር ከማስገባት የሚመነጭ ነው፡፡
 
ሰዶምና ገሞራን በእሳት ለማቃጠል የተላኩት መላእክት ወደ ሎጥ ቤት በገቡ ጊዜ ሎጥ በግምባሩ ተደፍቶ ለመላእክቱ እንደሰገደ ተጽፏል (ዘፍ. 19፥1)፡፡

ኢያሱ ወልደ ነዌ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በተገለጠለት ጊዜ በግምባሩ ተደፍቶ ለመልአኩ ሰግዶለታል፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል የተቃውሞ አነጋገር አልተናገረም፡፡ ‹‹የቆምክባት ሥፍራ የተቀደሰች መሬት ናትና ጫማህን ከእግርህ አውጣ›› ከማለት በስተቀር (መጽ ኢያሱ 5፥13)፡፡
 
የእሥራአል ንጉሥ የነበረው ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት ከእሥራኤል ሽማግሌዎች ጋር ከመሬት ከፍ ብሎ ሰይፉን ዘርግቶ ለተገለጠላቸው ለእግዚአብሔር መልአክ ሰግደውለታል (ዜና መዋዕል ቀዳ 21፥16)፡፡
 
ነቢየ እግዚአብሔር ዳንኤል መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በአባል ወንዝ አጠገብ በተገለጠበት ጊዜ ለመልአኩ ለቅዱስ ገብርኤል ራሱን ዝቅ አድርጐ በግንባሩ ወድቆ ሰግዶለታል፡፡ በዚሁም ላይ የግርማውን አስፈሪነት እና አስደንጋጭነት ጠቅሷል (ዳን. 8፥15)፡፡
 
ከላይ የተገለጹት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች የሚያስገነዝቡን ለመላእክት ቅዱሳን ሰዎች እንዴት አክብረው እንደሰገዱላቸው ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹የእግዚአብሐርን ቃል የተናገሩአቸሁን ዋሃቻችሁን አስቡ የኑሮአቸውንም ፍሮ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው›› (ዕብ. 13፥7) እንዳለው የቅዱሳን አባቶቻችንና ሕይወት አኗኗር ዛሬ ለእኛ መመሪያ ሊሆነን ይገባል፡፡ እነርሱ አድርገው የተጠቀሙበትን ሁሉ እኛም እናደርገዋለን፡፡ እነርሱ ለቅዱሳን መላእክት ያላቸውን ፍቅርና አክብሮት በስግደት እንደገለጹ እኛም እግዚአብሔር ላከበራቸው ቅዱሳን መላእክት ፍቅራችንንና አክብሮታችንን በሥዕላቸው ፊት በመንበርከክ በመስገድ እንገልጻለን፡፡
 
መላእክት ቢገለጡም ባይገለጡም ሕልውናቸው የተረጋገጠ ነውና ክብራቸው ያው ነው፡፡ ምናልባት አንዳንድ ሰዎች ሲገለጡ እንጂ ካልተገለጡ ሊሰገድላቸው አይገባም ሊሉ ይችላሉ፡፡ በዓይን ዓይቶ በእጅ ዳብሶ ከማመን ሳያዩ የሚያምኑ ብጹዓን እንደሆኑ ጌታችን አስተም…ል (ዮሐ. 2ዐ፥29)፡፡
 
ስለዚህ እነዚህ ቅዱሳን አባቶች በዓይናቸው ዓይተው፣ በጆሯቸው ሰምተው ያደረጉትን እና ያመኑትን ለእኛ በማስተላለፋቸው እኛም የእነርሱን ዓይን ዓይን አድርገን ማእነርሱ አይተዋቸው የሰጡትን ክብር እንሰጣቸዋለን፡፡ መገለጣቸውና አለመገለጣቸው በእግዚአብሔር ዘንድ ያላቸውን ክብር አይጨምረውም አይቀንሰውምና ክብራቸው አንድ ነው፡፡ ስለዚህ ይሰገድላቸው ዘንድ የሚገባ ከሆነ ሲገለጡ ሳይገለጡ የሚል ሁኔታ መፈጠር የለበትም፡፡ ለእግዚአብሔር በመንፈስ የአምልኮት ስግደት እንደምንሰግድ ሁሉ (ዮሐ. 4፥24) እግዚአብሔር ባለበት ቦታ ሁሉ አብረው ለሚገኙት ቅዱሳን መላእክትም የጸጋ ስግደት በእምነት ማቅረብ ይገባል፡፡ እነርሱም እግዚአብሐር ባለበት ቦታ ሁሉ አሉና፡፡


ራእ. 19፥10 (‹‹አትስገድልኝ››)

አንዳንዶች ተጠራጣሪዎች ደግሞ ለመላእክት ሲገለጡም ሆነ ሳይገለጡ ምንም ዓይነት ስግደት አይገባቸውም በማለት ራእ. 19፥10 (‹‹አትስገድልኝ››) ላይ ያለውን ይጠቅሳሉ፡፡ በመሠረቱ ይህ ጥቅስ ለመላእክት የጸጋ ስግደት መስግድ እንደሚገባን እንጂ መስገድ እንደማይገባን የሚገልጽ አይደለም፡፡ ወንጌላዊውና ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ለመልአኩ መስገዱ ሳያውቀው ሳይረዳው ያደረገው ድርጊት እንዳልሆነ እንድናምን ማንነቱና ሕይወቱ ያስገነዝበናል፡፡ ምክንያቱም የጥበብ፣ የማስተዋል፣ የዕውቀት ጸጋን የሚያድል መንፈስ ቅዱስ አድሮበት እያለ ሳያውቀው አደረገው ብሎ መናገርና ማመን መንፈስ ቅዱስን እንደ መጽረፍ /መስደብ/ ነው፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የተቃኘ ሰው የሚያመልከውንና የሚሠራውን ሁሉ የሚያውቅ ነው፡፡ በተለይ ቅዱስ ዮሐንስ አካል ከሕልውና ተገልጾለት ምሥጢረ መለኮትን የተናገረ ታላቅ ሰው ሆኖ ሳለ ትንሿ ጉዳይ ተሰውራው ለመልአኩ ሳያውቅ ሰግዶ ተግሳጽ ደረሰበት ብሎ ማመን ሞኝነት ብቻ ሳይሆን ክህደትም ጭምር ነው፡፡ የመንፈስ ቅዱስን ሰላም ማቃለል ነው፡፡ «መንፈስ ቅዱስ የሰደበ ደግሞ ኃጢአቱ አይሠረይለትም፡፡» (ማቴ. 12፥31-32)፡፡
 
የመልአኩ አነጋገር ታዲያ እንዴት ይተረጎማል? መልአኩ ቅዱስ ዮሐንስን አትስገድልኝ ማለቱ ስለ ሁለት ነገር ነው፡፡

1ኛ. ስለ ትኀትና

ዲያብሎስ ከሥልጣኑ የተሻረው ከክብሩ የተዋረደው በትዕቢቱ እንደሆነ የታወቀ ነው፡፡ ቅዱሳን መላእክት ግን ትሕትናን ገንዘብ ያደረጉ በመሆናቸው እንደ ሰይጣን ስገዱልን የሚሉ አይደሉም፡፡ ዳሩ ግን እግዚአብሔር ይከበሩ ዘንድ ፈቃዱ በመሆኑ የእግዚአብሔር ሰዎች እንዲወዷቸውና እንዲያከብåቸው አድርጓል፡፡ ለዮሐንስ በሰገደለት ጊዜ «አትስገድልኝ» ማለቱ በእግዚአብሔር ዘንድ የተጠላ ከአምልኮተ እግዚአብሔር የሚያወጣ ለጣኦት እንደመስገድ የሚያስቆጥር ሆኖ ሳይሆን መልአኩ ራሱን በዮሐንስ ፊት ዝቅ ከማድረጉ የተነሣ ስለ ትሕትና የተናገረው ነው፡፡ አንድ ሰው ሌላውን ሰው አክብሮ እጅ ቢነሣው /ከመቀመጫው ሲነሳና ሲቀበለው/ éረ አይገባም እንደሚለው ሁሉ ማለት ነው፡፡ ለዚሁም ማረጋገጫ የሚሆነን (ለትሕትና የተናገረ መሆኑን) በምዕራፍ 19 የሰጠውን ማስጠንቀቂያ በምዕራፍ 21 ላይ መድገሙ ነው፡፡ ለትሕትና የተናገረው መሆኑን ያወቀው ዮሐንስ ለመልአኩ ክብር መስጠት እንዳለበትና መስገድ እንደሚገባው ዐውቆ ድጋሚ ሲገለጥለት በድጋሚ ሰግዶለታል፡፡

2ኛ ስለ ሥልጣነ ክህነት ክብር ሲል

የቤተ ክርስቲያን የአጥቢያ ኮከብ ቅዱስ ጳውሎስ የካህናትን ሥልጣን አስመልክቶ ሲያስተምር #ካህናት ሰውን ሁሉ እንደሚዳኙ አታውቁምን? እናንተ ሰውን ሁሉ የምትዳኙ ከሆናችሁ ይህን ትንሹን ነገር ልትፈርዱ አይገባችሁምን? የዚህንስ ዓለም ዳኝነት ተውትና መላእክትን ስንኳ እንድንገዛ አታውቁምን$ (1ቆሮ 6፥2-3) ብሏል፡፡
 
ከዚህ ትምህርቱ የምገነዘበው ካህናት በሥልጣናቸው መላእክትን ስንኳ ሳይቀር እንደሚያዙ ነው፡፡ ይህንንም ከቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርት እንረዳለን፡፡ በ344 ዓ.ም. በአንጾኪያ ከተማ የተወለደው ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እምነትንና ፍቅርን፣ ትዕግሥትንና ትሕትናን፣ በአንድነት ገመድ አስሮ ሕዝቡን ለ7 ዓመት ወንጌልን ሰብኳል፡፡ በ387 ዓ.ም. በአንጾኪያ ከተማ ፖትርያርክነት ተሾሞ ሳለ አንድ ጉዳይ ይገጥመዋል፡፡
 
ንጉሡ አርቃድዮስና ንግሥቲቱ አውዶክያስ ልጅ እየወለዱ እየሞተባቸው አላድግ ስላላቸው የዚህን ምክንያት ቢጠይቁ ደግ ሰው ክርስትና ባያነሣላችሁ ይሆናል ስላሏቸው ከዮሐንስ አፈወርቅ የበለጠ ደግ ሰው በዘመናችን አለን? በማለት ሴት ልጅ በወለዱ ጊዜ መጥተህ ክርስትና አንሣልን ብለው ላኩበት እርሱም ጥሪውን አክብሮ ሲሆድ በመንገድ ከእግዚአብሔር ዘንድ ከተላከ መልአክ ጋር ይገናኛል፡፡ የበቃ ነውና ረቂቁን መልአክ ሊያየው ችሏል፡፡ ዮሐንስም መልአኩን ‹‹ወዴት ትሄዳለህ?›› ብሎ ጠየቀው መልአኩም ሲመልስለት ‹‹አሁን አንተ የምትሄድባትን ብላቴና ነፍሷን ከሥጋዋ ለይተህ አምጣ ብሎኝ የታዘዝኩትን ለመፈጸም ወደዚያ መሄዴ ነው›› ይለዋል፡፡ ዮሐንስም ‹‹ቆየኝ በጥምቀት ሀብተ ውልድና፣ ስመ ክርስትና ከተሰጣት በኋላ የታዘዝከውን ትፈጽማለህ፡፡ እስከዚያው ግን ከዚሁ አትንቀሳቀስ›› ብሎት በሥልጣነ ክህነቱ ገዝቶት ሄደ፡፡ መልአኩም የዮሐንስን ግዝት ጠብቆ ባለበት ቆመ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ልጅቷን ካጠመቃት በኋላ ንግቶት በሌላ መንገድ ተመለሰ፡፡

የካህናት ሥልጣናቸው የማይናቅ፣ ትእዛዛቸውም ክብር የሚገባው መሆኑን ስለሚያውቅ ያ መልአክ ወደ ላይም ወደታችም ሳይል አሥር ዓመት ከዚያው ሥፍራ ቆሞ ኖረ፡፡ አሥር ዓመት ሲሆናት ለባል ታጨች ያጠመቅካት ብላቴና እነሆ ለአቅመ ሔዋን፣ ባል ልታገባ ነውና መጥተህ ባርከህ ስደዳት ብለው ለዮሐንስ አፈወርቅ ላኩበት፡፡ እርሱም በጥሪው መሠረት ከዛሬ አሥር ዓመት ልጅቱን ሊያጠምቅ ሲሔድ በሄደበት መንገድ መልአኩን ቆሞ አገኘው፡፡ «ምነው ከዚህ ቆመሃል?» አለው፡፡ መልአኩም ሲመልስለት «የካህናት ማዕረጋቸው የከበረ ነውና መች ወዲያ ወዲህ ያሰኛል፡፡ ቃልህን አክብሬ አንተ ቆይ ካልከኝ ወዲያና ወዲህ ብዬ አላውቅም» አለው ቅዱስ ዮሐንስም በዝንጉዕነቱ ራሱን ወቅሶ መልአኩን የታዘዘውን ያደርግ ዘንድ አሰናብቶታል፡፡

ከላይ በተገለጸው ታሪክ ብናይ በፍጥሞ ደሴት መልአኩ ለዮሐንስ ወንጌላዊ አትስገድልኝ ማለቱ ዮሐንስ ካህንም ነውና ሥልጣኑ ሊያከብር እንደሚገባው ለመግለጽ ሽቶ ነው፡፡ በክብር ዮሐንስ ከመልአኩ ይበልጣልና፡፡




[1] /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት ገጽ 743/
 


Written By: admin
Date Posted: 12/19/2007
Number of Views: 14689

Return

  
Copyright 2016 by Mahibere Kidusan USA Center  | Terms Of Use | Privacy Statement